መዝሙር 42
42
ሁለተኛ መጽሐፍ
ከመዝሙር 42–72
መዝሙር 42#42 በብዙ የዕብራይስጥ ቅጆች መዝሙር 42 እና 43 አንድ መዝሙር ነው።
ለመዘምራን አለቃ።
በስደት ላይ ያለ ሌዋዊ ልቅሶ
1ዋላ የምንጭ ውሃ እንደምትናፍቅ፣
አምላክ ሆይ፤ ነፍሴም እንዲሁ አንተን ትናፍቃለች።
2ነፍሴ አምላክን፣ ሕያው አምላክን ተጠማች፤
መቼ ደርሼ ነው የአምላክን ፊት የማየው?
3ሰዎች ቀኑን ሙሉ፣
“አምላክህ የት አለ?” ባሉኝ ቍጥር፣
እንባዬ ቀንና ሌሊት፣
ምግብ ሆነኝ።
4ነፍሴ በውስጤ እየፈሰሰች፣
እነዚህን ነገሮች አስታወስሁኝ፤
ታላቅ ሕዝብ ወደ እግዚአብሔር ቤት እየመራሁ፣
በእልልታና በምስጋና መዝሙር፣
በአእላፍ ሕዝብ መካከል፣
እንዴት ከሕዝቡ ጋር እሄድ እንደ ነበር ትዝ አለኝ።
5ነፍሴ ሆይ፤ ለምን ትተክዢያለሽ?
ለምንስ በውስጤ ትታወኪያለሽ?
ተስፋሽን በአምላክ ላይ አድርጊ፤
6አዳኜና አምላኬን፣ ገና አመሰግነዋለሁና።
ነፍሴ በውስጤ ተክዛለች፤
ስለዚህ በዮርዳኖስ ምድር፣
በአርሞንኤም ከፍታ፣ በሚዛር ተራራ ዐስብሃለሁ።
7በፏፏቴህ ማስገምገም፣
አንዱ ጥልቅ ሌላውን ጥልቅ ይጣራል፤
ማዕበልህና ሞገድህ ሁሉ፣
ሙሉ በሙሉ አጥለቀለቀኝ።
8 እግዚአብሔር ምሕረቱን በቀን ያዝዛል፤
ዝማሬውም በሌሊት በእኔ ዘንድ አለ፤
ይህም ለሕይወቴ አምላክ የማቀርበው ጸሎት ነው።
9እግዚአብሔር ዐለቴን፣
“ለምን ረሳኸኝ?
ጠላትስ እያስጨነቀኝ፣
ለምን በሐዘን እመላለሳለሁ?” እለዋለሁ።
10ጠላቶቼ ቀኑን ሙሉ፣
“አምላክህ የት አለ?” እያሉ፣
በነገር ጠዘጠዙኝ፣
ዐጥንቴም ደቀቀ።
11ነፍሴ ሆይ፤ ለምን ትተክዢያለሽ?
ለምንስ በውስጤ ትታወኪያለሽ?
ተስፋሽን በአምላክ ላይ አድርጊ፣
አዳኜና አምላኬን
ገና አመሰግነዋለሁና።
Currently Selected:
መዝሙር 42: NASV
Highlight
Share
Copy
Want to have your highlights saved across all your devices? Sign up or sign in
መጽሐፍ ቅዱስ፣ አዲሱ መደበኛ ትርጕም™
የቅጅ መብት © 2001 በ Biblica, Inc.
ፈቃድ የተገኘባቸው ናቸው። መብቱ በመላው ዓለም በሕግ የተጠበቀ።
Holy Bible, New Amharic Standard Version™ (Addisu Medebegna Tirgum™)
Copyright © 2001 by Biblica, Inc.
Used with permission. All rights reserved worldwide.