“ለእግዚአብሔር የሚያቀርቡት የደኅንነት መሥዋዕት ሕግ ይህ ነው። ለምስጋና ቢያቀርበው፥ ከምስጋናው መሥዋዕት ጋር በዘይት የተለወሰ የቂጣ እንጎቻ፥ በዘይትም የተቀባ ስስ ቂጣ፥ በዘይትም የተለወሰ መልካም የስንዴ ዱቄት ያቀርባል። ለምስጋና የሚሆነውን የደኅንነት መሥዋዕት በአቀረበ ጊዜ እርሾ ያለበትን ኅብስት ያቀርባል። ከቍርባኑም ሁሉ የእግዚአብሔርን ድርሻ ከእነርሱ አንዱን ያነሣል። እርሱም የደኅንነትን መሥዋዕት ደም ለሚረጨው ካህን ይሆናል። “ለምስጋና የሚሆነው የደኅንነት መሥዋዕት ሥጋም ለእርሱ ነው፤ በሚቀርብበትም ቀን ይበሉታል፤ ከእርሱ እስከ ነገ ምንም አያተርፉም። የቍርባኑም መሥዋዕት የስእለት ወይም የፈቃድ ቢሆን፥ መሥዋዕቱ በሚቀርብበት ቀን ይብሉት፤ ከእርሱም የቀረውን በነጋው ይብሉት፤ ከመሥዋዕቱም ሥጋ እስከ ሦስተኛው ቀን የሚቈየውን በእሳት ያቃጥሉታል። በሦስተኛው ቀን ከደኅንነት መሥዋዕት ሥጋ ቢበላ፥ አይሠምርም፤ ላቀረበው ሰው የተጠላ ይሆንበታል እንጂ ቍርባን ሆኖ አይቈጠርለትም፤ ከእርሱም የበላ ሰው ኀጢአቱን ይሸከማል። “ርኩስ ነገር የሚነካውን ሥጋ አይብሉት፤ በእሳት ያቃጥሉት እንጂ። ንጹሕ የሆነ ሰው ሁሉ ግን ከሥጋው ይብላ። ኀጢአት ሳለባት፥ ለእግዚአብሔር ከሆነው ከደኅንነት መሥዋዕት ሥጋ የበላች ሰውነት፥ ያች ሰውነት ከሕዝብዋ ተለይታ ትጥፋ። ከርኩስ ሁሉ፥ ወይም ከረከሰው ሰው፥ ወይም ንጹሕ ካልሆነው እንስሳ የነካች ሰውነት፥ ለእግዚአብሔር ከሆነው ከደኅንነት መሥዋዕት ሥጋ ብትበላ፥ ያች ሰውነት ከሕዝብዋ ተለይታ ትጥፋ።” እግዚአብሔርም ሙሴን እንዲህ ብሎ ተናገረው፦ “የእስራኤልን ልጆች እንዲህ ብለህ ተናገራቸው፦ የበሬ ወይም የበግ ወይም የፍየል ስብ ከቶ አትብሉ። የሞተውን ስብ፥ አውሬ የሰበረውንም ስብ ለሌላ ተግባር አድርጉት፤ እናንተ ግን አትብሉት፤ ለእግዚአብሔር በእሳት ከሚቀርበው ከእንስሳ ስብ የሚበላ ሁሉ ያች የበላች ሰውነት ከሕዝብዋ ተለይታ ትጥፋ። በመኖሪያዎቻችሁ ሁሉ የወፍ ወይም የእንስሳ ደም ቢሆን አትብሉ። ደም የምትበላ ሰውነት ሁሉ ያች ሰውነት ከሕዝብዋ ተለይታ ትጥፋ።” እግዚአብሔርም ሙሴን እንዲህ ብሎ ተናገረው፦ “የእስራኤልን ልጆች እንዲህ ብለህ ተናገራቸው፦ ለእግዚአብሔር የደኅንነት መሥዋዕት የሚያቀርብ ሰው ቍርባኑን ለእግዚአብሔር ከደኅንነቱ መሥዋዕት ያመጣል። የእርሱ እጆች ለእግዚአብሔር የእሳቱን ቍርባን ያመጣሉ፤ ፍርምባውን በእግዚአብሔር ፊት ቍርባን ያቀርብ ዘንድ በጉበቱ ላይ ያለውን መረብና የፍርምባውን ስብ ያመጣል። ካህኑም ስቡን በመሠዊያው ላይ ይጨምረው፤ ፍርምባውም ለአሮንና ለልጆቹ ይሁን። ከደኅንነት መሥዋዕታችሁ ቀኝ ወርቹን ለማንሣት ቍርባን እንዲሆን ለካህኑ ትሰጡታላቸሁ። ከአሮንም ልጆች የደኅንነትን መሥዋዕት ደሙንና ስቡን ለሚያቀርብ ለእርሱ ቀኝ ወርቹ እድል ፈንታው ይሆናል። ፍርምባውንና የቀኝ ወርቹን ከእስራኤል ልጆች ከደኅንነት መሥዋዕታቸው ወስጄአለሁ፤ ለካህኑ ለአሮንና ለልጆቹም ለዘለዓለም ሕግ እንዲሆን ከእስራኤል ልጆች ዘንድ ሰጥቼአቸዋለሁ።” እግዚአብሔርን በክህነት ያገለግሉት ዘንድ በተቀቡበት ቀን ለእግዚአብሔር ከሆነ ከእሳት ቍርባን የአሮንና የልጆቹ ሕግ ይህ ነው። ለልጅ ልጃቸው ለዘለዓለም ሕግ እንዲሆን በቀባቸው ቀን የእስራኤል ልጆች ይሰጡአቸው ዘንድ እግዚአብሔር ያዘዘው ይህ ነው። የሚቃጠል መሥዋዕትና የእህል ቍርባን፥ የኀጢአትና የበደል መሥዋዕት፥ የቅድስናና የደኅንነት መሥዋዕት ሕግ ይህ ነው። እግዚአብሔር በሲና ምድረ በዳ ቍርባናቸውን በእግዚአብሔር ፊት ያቀርቡ ዘንድ ለእስራኤል ልጆች ባዘዘ ጊዜ በሲና ተራራ ለሙሴ ያዘዘው ይህ ነው።
ኦሪት ዘሌዋውያን 7 ያንብቡ
ያጋሩ
ሁሉንም ሥሪቶች ያነጻጽሩ: ኦሪት ዘሌዋውያን 7:11-38
ጥቅሶችን ያስቀምጡ፣ ያለበይነመረብ ያንብቡ፣ አጫጭር የትምህርት ቪዲዮዎችን ይመልከቱ እና ሌሎችም!
ቤት
መጽሐፍ ቅዱስ
እቅዶች
ቪዲዮዎች