“ስለ ሕዝቡም ኀጢአት የሚሠዋውን መሥዋዕት ፍየል ያርዳል፤ ደሙንም ወደ መጋረጃው ውስጥ ያመጣዋል፤ በወይፈኑም ደም እንዳደረገ በፍየሉ ደም ያደርጋል፤ በመክደኛው ላይና በመክደኛው ፊት ይረጨዋል። ከእስራኤል ልጆች ርኩስነት፥ ከመተላለፋቸውም፥ ከኀጢአታቸውም የተነሣ ለመቅደሱ ያስተሰርይለታል፤ እንዲሁም በርኩስነታቸው መካከል ከእነርሱ ጋር ለኖረች ለምስክሩ ድንኳን ያደርጋል። እርሱ ለማስተስረይ ወደ መቅደሱ በገባ ጊዜ ለራሱ፥ ለቤተሰቡም፥ ለእስራኤል ጉባኤ ሁሉ አስተስርዮ እስኪወጣ ድረስ በምስክሩ ድንኳን ውስጥ ማንም አይኖርም። በእግዚአብሔርም ፊት ወዳለው ወደ መሠዊያው ወጥቶ ያስተሰርይለታል፤ ከወይፈኑም ደም፥ ከፍየሉም ደም ወስዶ በመሠዊያው ዙሪያ ያሉትን ቀንዶች ያስነካል። ከደሙም በእርሱ ላይ ሰባት ጊዜ በጣቱ ይረጫል፤ ከእስራኤልም ልጆች ርኩስነት ያነጻዋል፤ ይቀድሰውማል። “ስለመቅደሱ፥ስለ ምስክሩም ድንኳን፥ ስለ መሠዊያውም ማስተስረያና ስለ ካህናትም ማንጻት ከፈጸመ በኋላ ደኅነኛውን ፍየል ያቀርባል። አሮንም ሁለቱን እጆቹን በደኅነኛው ፍየል ራስ ላይ ይጭናል፤ በላዩም የእስራኤልን ልጆች በደል ሁሉ፥ መተላለፋቸውን ሁሉ፥ ኀጢአታቸውንም ሁሉ ያስተሰርያል፤ በፍየሉም ራስ ላይ ያሸክመዋል፤ በተዘጋጀው ሰውም እጅ ወደ ምድረ በዳ ይሰድደዋል። ፍየሉም ኀጢአታቸውን ሁሉ ወደ በረሃ ይሸከማል፤ ፍየሉንም ዛፍ በሌለበት በምድረ በዳ ውስጥ ይለቅቀዋል። “አሮንም ወደ ምስክሩ ድንኳን ይገባል፤ ወደ መቅደሱም በገባ ጊዜ የለበሰውን የተልባ እግር ልብስ ያወልቃል፤ በዚያም ይተወዋል። በተቀደሰውም ስፍራ ገላውን በውኃ ይታጠባል፤ ሌላውንም ልብስ ለብሶ ይወጣል፤ የእርሱንም የሚቃጠል መሥዋዕት ያቀርባል፤ ለካህናቱ እንዳስተሰረየ ለራሱም፥ ለሕዝቡም ያስተሰርያል። የኀጢአቱንም መሥዋዕት ስብ በመሠዊያው ላይ ያቃጥለዋል። ለመለቀቅ የሚሆነውን ፍየል የወሰደ ሰው ልብሱን ያጥባል፤ ገላውንም በውኃ ይታጠባል፤ ከዚያም በኋላ ወደ ሰፈሩ ይገባል። ለማስተስረያም እንዲሆን ደማቸው ወደ መቅደስ የገባውን የኀጢአቱን መሥዋዕት ወይፈንና የኀጢአቱን መሥዋዕት ፍየል ከሰፈሩ ወደ ውጭ ያወጡአቸዋል፤ ቍርበታቸውንም፥ ሥጋቸውንም፥ ፈርሳቸውንም በእሳት ያቃጥላሉ። ያቃጠላቸውም ሰው ልብሱን ያጥባል፤ ገላውንም በውኃ ይታጠባል፤ ከዚያም በኋላ ወደ ሰፈር ይገባል። “ይህም የዘለዓለም ሥርዐት ይሁንላችሁ። በዚህ ቀን ትነጹ ዘንድ ማስተስረያ ይሆንላችኋልና በሰባተኛው ወር ከወሩም በዐሥረኛው ቀን ራሳችሁን አስጨንቋት፤ የሀገር ልጅም፥ በእናንተም መካከል የተቀመጠ እንግዳ ሥራን ሁሉ አትሥሩበት፤ በእግዚአብሔርም ፊት ከኀጢአታችሁ ሁሉ ትነጻላችሁ። ታላቅ ሰንበት ይሆንላችኋል፤ ራሳችሁንም ታዋርዳላችሁ፤ የዘለዓለም ሥርዐት ነው። የሚቀባውም፥ በአባቱም ፋንታ ካህን ሊሆን የሚካነው ካህን ያስተስርይ፤ የተቀደሰውንም የተልባ እግር ልብስ ይልበስ። ለቅድስተ ቅዱሳንም ያስተስርይ፤ ለምስክሩ ድንኳን፥ ለመሠዊያውም ያስተስርይ፤ ለካህናቱም፥ ለጉባኤውም ሕዝብ ሁሉ ያስተስርይ። ይህም አንድ ጊዜ በዓመት ለእስራኤል ልጆች ስለ ኀጢአታቸው ሁሉ ያስተሰርይ ዘንድ የዘለዓለም ሥርዐት ይሁንላችሁ።” እግዚአብሔርም ሙሴን እንዳዘዘው እንዲሁ አደረገ።
ኦሪት ዘሌዋውያን 16 ያንብቡ
ያጋሩ
ሁሉንም ሥሪቶች ያነጻጽሩ: ኦሪት ዘሌዋውያን 16:15-34
ጥቅሶችን ያስቀምጡ፣ ያለበይነመረብ ያንብቡ፣ አጫጭር የትምህርት ቪዲዮዎችን ይመልከቱ እና ሌሎችም!
ቤት
መጽሐፍ ቅዱስ
እቅዶች
ቪዲዮዎች