ሉቃስ 7:1-10

ሉቃስ 7:1-10 NASV

ኢየሱስ ይህን ሁሉ በሕዝቡ ፊት ተናግሮ ከጨረሰ በኋላ ወደ ቅፍርናሆም ገባ። በዚያም አንድ የመቶ አለቃ ነበረ፤ እጅግ የሚወድደው ባሪያውም ታምሞበት ለሞት ተቃርቦ ነበር። እርሱም ስለ ኢየሱስ በሰማ ጊዜ፣ ባሪያውን መጥቶ እንዲፈውስለት ይለምኑት ዘንድ አንዳንድ የአይሁድ ሽማግሌዎችን ላከበት። መልእክተኞቹም ወደ ኢየሱስ በመጡ ጊዜ እንዲህ ብለው አጥብቀው ለመኑት፤ “ይህን ልታደርግለት ይገባዋል፤ ምክንያቱም ይህ ሰው ሕዝባችንን ይወድዳል፤ ምኵራባችንንም ያሠራልን እርሱ ነው።” ኢየሱስም ከእነርሱ ጋራ ሄደ። እርሱም ወደ ቤቱ በተቃረበ ጊዜ፣ የመቶ አለቃው ወዳጆቹን ልኮ እንዲህ አለው፤ “ጌታ ሆይ፤ ከቤቴ ጣራ በታች ልትገባ የሚገባኝ ሰው አይደለሁምና አትድከም፤ ከዚህም የተነሣ በአንተ ፊት ለመቅረብ እንኳ እንደሚገባኝ ራሴን አልቈጠርሁም፤ ብቻ አንድ ቃል ተናገር፤ ብላቴናዬም ይፈወሳል። እኔ ራሴ የበላይ አለቃ አለኝ፤ ከበታቼም የማዝዛቸው ወታደሮች አሉኝ፤ አንዱን፣ ‘ሂድ’ ስለው ይሄዳል፤ ሌላውን፣ ‘ና’ ስለው ይመጣል፤ ባሪያዬንም፣ ‘ይህን አድርግ’ ስለው ያደርጋል።” ኢየሱስም ይህን ሲሰማ በርሱ ተደነቀ፤ ዘወር ብሎም ይከተለው ለነበረው ሕዝብ፣ “እላችኋለሁ፤ እንዲህ ያለ ትልቅ እምነት በእስራኤል እንኳ አላገኘሁም” አላቸው። የተላኩት ሰዎችም ወደ ቤት በተመለሱ ጊዜ፣ ባሪያውን ድኖ አገኙት።