ኢሳይያስ 41:19-29

ኢሳይያስ 41:19-29 NASV

በምድረ በዳ፣ ዝግባን፣ ግራርን፣ ባርሰነትንና ወይራን አበቅላለሁ፤ በበረሓ፣ ጥድን፣ አስታንና ሸውሸዌን በአንድነት እተክላለሁ። ስለዚህ ሰዎች ያያሉ፤ ያውቃሉ፤ የእግዚአብሔር እጅ ይህን እንዳደረገ፣ የእስራኤል ቅዱስ እንደ ፈጠረው፣ በአንድነት ይገነዘባሉ፤ ያስተውላሉም። “ሙግታችሁን ይዛችሁ ቅረቡ” ይላል እግዚአብሔር፤ “ማስረጃችሁን አምጡ” ይላል የያዕቆብ ንጉሥ። “የሚሆነውን እንዲነግሩን፣ ጣዖቶቻችሁን አምጡ፤ እንድንገነዘብ፣ ፍጻሜአቸውን እንድናውቅ፣ የቀደሙት ነገሮች ምን እንደ ነበሩ ንገሩን፤ ስለሚመጡትም ነገሮች ግለጹልን። እናንተ አማልክት መሆናችሁን እናውቅ ዘንድ፣ ወደ ፊት ስለሚሆነው ንገሩን፤ እንድንደነግጥ፣ በፍርሀት እንድንዋጥ፣ መልካምም ሆነ ክፉ፣ አንድ ነገር አድርጉ። እነሆ፤ እናንተ ከምንም የማትቈጠሩ ናችሁ፤ ሥራችሁ ፈጽሞ ዋጋ ቢስ ነው፤ የመረጣችሁም አስጸያፊ ነው። “አንዱን ከሰሜን አስነሣሁት፤ እርሱም ይመጣል፤ ከፀሓይ መውጫ የሚመጣው፣ ስሜን የሚጠራ ነው፤ ሸክላ ሠሪ ዐፈር እንደሚረግጥ፣ አለቆችን እንዲሁ እንደ ጭቃ ይረግጣል። እኛ እናውቅ ዘንድ ይህን ከመጀመሪያው የተናገረ፣ ‘እርሱ ትክክል ነው’ እንልም ዘንድ ቀድሞ የተናገረ ማነው? ማንም አልተናገረም፤ ቀደም ብሎ የተናገረ የለም፤ ቃላችሁንም የሰማ የለም። በመጀመሪያ፣ ‘እነሆ፤ ተመልከቺአቸው!’ ብዬ ለጽዮን የተናገርሁ እኔ ነበርሁ፤ ለኢየሩሳሌምም የምሥራች ነጋሪን ሰጥቻለሁ። ተመለከትሁ ማንም አልነበረም፤ ከመካከላቸው አማካሪ የለም፤ ስጠይቅም መልስ የሚሰጥ የለም። እነሆ፤ ሁሉም ከንቱ ናቸው! ሥራቸውም መና ነው፤ ምስሎቻቸውም ባዶ ነፋስ ናቸው።