YouVersion Logo
Search Icon

ወደ ፊልጵስዩስ ሰዎች መግቢያ

መግቢያ
ጳውሎስ ይህን መልእክት የጻፈው፥ መቄዶንያ በሚባለው የሮም ግዛት በምትገኘው በፊልጵስዩስ ላለችው ቤተ ክርስቲያን ነው፤ ይህች ቤተ ክርስቲያን፥ ጳውሎስ በአውሮፓ ምድር በመጀመሪያ ያቋቋማት ናት፤ መልእክቱ የተጻፈው ጳውሎስ እስር ቤት በነበረበት፥ ከሌሎች ክርስቲያን አገልጋዮች ተቃውሞ በደረሰበት ጊዜና በፊልጵስዩስ ቤተ ክርስቲያን በተነሣው የሐሰት ትምህርት ምክንያት ልቡ በሐዘን በተሰበረበት ወቅት ነው። ይሁን እንጂ ጳውሎስ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ያለው እምነት እጅግ የጠለቀ በመሆኑ በዚህ መልእክት ጐልቶ የሚታየው ደስታና ሙሉ መተማመን ነው።
ጳውሎስ ይህን መልእክት የጻፈበት ተቀዳሚ ምክንያት በችግሩ ጊዜ እርሱን ለመርዳት ስጦታ ልከውለት ስለ ነበር የፊልጵስዩስን ምእመናን ለማመስገን ነው፤ በእርሱም ሆነ በእነርሱ ላይ ልዩ ልዩ ችግሮች የደረሱ ቢሆኑም እንኳ ድፍረትና ሙሉ መተማመን እንዲኖራቸው በዚህ አጋጣሚ ያበረታታቸዋል። ትዕቢትንና ትምክሕትን አስወግደው በኢየሱስ ክርስቶስ ትሕትና እንዲሞሉ በጥብቅ ያሳስባቸዋል፤ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር በመንፈስ አንድ በመሆን ያገኙት ሕይወት ከእግዚአብሔር የጸጋ ስጦታ የመነጨና በእምነት የተቀበሉት ነው እንጂ ሕግን በመፈጸም የተገኘ አይደለም በማለት ያስታውሳቸዋል፤ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር በመተባበር ለሚኖሩ ሁሉ እግዚአብሔር ስለሚሰጣቸው ሰላምና ደስታም ይጽፍላቸዋል።
ይህ መልእክት የሚታወቀው ደስታን፥ መተማመንን፥ ኅብረትንና በክርስትና እምነትና ሕይወት መጽናትን አጒልቶ በማሳየቱ ነው፤ በተጨማሪም ሐዋርያው ጳውሎስ ለፊልጵስዩስ ቤተ ክርስቲያን ያለውን ታላቅ ፍቅር ይገልጣል።
አጠቃላይ የመጽሐፉ ይዘት
መግቢያ 1፥1-11
ጳውሎስ የነበረበት ግላዊ ሁኔታ 1፥12-26
የክርስትና ሕይወት ምሳሌ 1፥27—2፥18
ለጢሞቴዎስና ለኤጳፍሮዲቱስ ዕቅድ 2፥19-30
ከእምነት ተቃዋሚዎች ማስጠንቀቂያ 3፥1—4፥9
ጳውሎስ ለፊልጵስዩስ ክርስቲያኖች ያቀረበው ምስጋናና ምክር 4፥10-20
ማጠቃለያ 4፥21-23

Highlight

Share

Copy

None

Want to have your highlights saved across all your devices? Sign up or sign in