YouVersion Logo
Search Icon

መዝሙር 140

140
መዝሙር 140
በክፉዎች ላይ የቀረበ ጸሎት
ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር።
1 እግዚአብሔር ሆይ፤ ከክፉ ሰዎች አድነኝ፤
ከዐመፀኞችም ሰዎች ጠብቀኝ፤
2እነርሱ በልባቸው ክፉ ነገር ያውጠነጥናሉ፤
በየዕለቱም ጦርነት ይጭራሉ።
3ምላሳቸውን እንደ እባብ ያሾላሉ፤
ከከንፈራቸውም በታች የእፉኝት መርዝ አለ። ሴላ
4 እግዚአብሔር ሆይ፤ ከክፉዎች እጅ ጠብቀኝ፤
እግሮቼንም ለመጥለፍ ከሚያደቡ ዐመፀኞች ሰውረኝ።
5ትዕቢተኞች ወጥመድ በስውር አስቀመጡብኝ፤
የመረባቸውን ገመድ ዘረጉብኝ፤
በመንገዴም ላይ አሽክላ አኖሩ። ሴላ
6 እግዚአብሔር ሆይ፤ “አንተ አምላኬ ነህ” እልሃለሁ፤
እግዚአብሔር ሆይ፤ የልመና ጩኸቴን ስማ።
7ብርቱ አዳኝ የሆንህ ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፤
በጦርነት ዕለት የራስ ቍር ሆንኸኝ።
8 እግዚአብሔር ሆይ፤ የክፉዎች ምኞት አይፈጸም፤
በትዕቢትም እንዳይኵራሩ፣
ዕቅዳቸው አይሳካ። ሴላ
9ዙሪያዬን የከበቡኝ ሰዎች ራስ፣
የከንፈራቸው መዘዝ ይጠምጠምበት።
10የእሳት ፍም በላያቸው ይውረድ፤
ዳግመኛም እንዳይነሡ ወደ እሳት ይጣሉ፤
ማጥ ወዳለበት ጕድጓድ ይውደቁ።
11ምላሰኛ በምድሪቱ ጸንቶ አይኑር፤
ዐመፀኛውን ሰው ክፋት አሳድዶ ያጥፋው።
12 እግዚአብሔር ለድኻ ፍትሕን እንደሚያስከብር፣
ለችግረኛውም ትክክለኛ ፍርድን እንደሚሰጥ ዐውቃለሁ።
13ጻድቃን በእውነት ስምህን ያመሰግናሉ፤
ቅኖችም በፊትህ ይኖራሉ።

Currently Selected:

መዝሙር 140: NASV

Highlight

Share

Copy

None

Want to have your highlights saved across all your devices? Sign up or sign in