ኦሪት ዘሌዋውያን 27
27
ለእግዚአብሔር ስለሚቀርበው መባእ የተሰጠ ሕግ
1እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ ብሎ ተናገረው፦ 2“ለእስራኤል ልጆች እንዲህ ብለህ ንገራቸው፦ ማናቸውም ሰው ስለ ነፍሱ ቤዛ ለእግዚአብሔር ስእለት ቢሳል አንተ እንደምትገምተው መጠን ስለ ሰውነቱ ዋጋውን ይስጥ። 3ለወንድ ከሃያ ዓመት ጀምሮ እስከ ስድሳ ዓመት ድረስ እንደ መቅደሱ ሚዛን ግምቱ አምሳ የብር ዲድርክም ይሁን። 4ሴትም ብትሆን ግምቷ ሠላሳ የብር ዲድርክም ይሁን። 5ከአምስት ዓመትም ጀምሮ እስከ ሃያ ዓመት ድረስ ግምቱ ለወንድ ሃያ የብር ዲድርክም፥ ለሴትም ዐሥር የብር ዲድርክም ይሁን። 6ከአንድ ወርም እስከ አምስት ዓመት ድረስ ለወንድ ግምቱ አምስት የብር ዲድርክም፥ ለሴትም ግምቷ ሦስት የብር ዲድርክም ይሁን። 7ከስድሳ ዓመትም ጀምሮ ከዚያም በላይ ወንድ ቢሆን ግምቱ ዐሥራ አምስት ዲድርክም፥ ለሴትም ዐሥር ዲድርክም ይሁን። 8ለግምቱ የሚከፍለውን ቢያጣ ግን በካህኑ ፊት ይቁም፤ ካህኑም የተሳለውን ሰው ከእጁ ባለው ገንዘብ መጠን ይገምትለት፤ ካህኑም የተሳለው ሰው እንደሚችል መጠን ይገምትለት።
9“ለእግዚአብሔርም መሥዋዕት አድርጎ የሚያቀርበው እንስሳ ቢሆን፥ ሰው ከእነዚህ ለእግዚአብሔር የሚሰጠው ሁሉ ቅዱስ ይሆናል። 10መልካሙን በክፉ፥ ክፉውንም በመልካም አይለውጥ፤ እንስሳንም በእንስሳ ቢለውጥ እርሱና ልዋጩ የተቀደሱ ይሆናሉ። 11እንስሳው ለእግዚአብሔር መሥዋዕት መሆን የማይገባው ርኩስ ቢሆን፥ እንስሳውን በካህኑ ፊት ያቁመው። 12መልካምም ቢሆን ክፉም ቢሆን ካህኑ ይገምተው፤ ካህኑም እንደሚገምተው መጠን እንዲሁ ይሁን። 13ይቤዠው ዘንድ ቢወድድ ግን ከግምቱ በላይ አምስተኛ እጅ ይጨምር።
14“ሰውም ለእግዚአብሔር ቅዱስ ይሆን ዘንድ ቤቱን ቢቀድስ፥ ካህኑ መልካም ወይም ክፉ እንደ ሆነ ይገምተዋል፤ ካህኑም እንደሚገምተው መጠን እንዲሁ ይቆማል። 15የተሳለውም ሰው ቤቱን ይቤዠው ዘንድ ቢወድድ ከግምቱ ገንዘብ በላይ አምስተኛ እጅ ይጨምር፤ ቤቱም ለእርሱ ይሆናል።
16“ሰውም ከርስቱ እርሻ ለእግዚአብሔር ቢሳል፥ እንደ መዘራቱ መጠን ይገመት፤ አንድ የቆሮስ መስፈሪያ ገብስ የሚዘራበት እርሻ አምሳ ወቄት ብር ይገመታል። 17እርሻውንም ከኢዮቤልዩ ዓመት ጀምሮ ቢሳል፥ እንደ ግምቱ መጠን ይቆማል። 18እርሻውንም ከኢዮቤልዩ ዓመት በኋላ ቢሳል፥ ካህኑ እስከ ኢዮቤልዩ ዓመት ድረስ እንደ ቀሩት ዓመታት ገንዘቡን ይቈጥርለታል፤ ከግምቱም ይጐድላል። 19እርሻውንም የተሳለ ሰው ይቤዠው ዘንድ ቢወድድ፥ ከግምቱ ገንዘብ በላይ አምስተኛ እጅ ይጨምር፤ ለእርሱም ይሆናል። 20እርሻውንም ባይቤዠው፥ ወይም ለሌላ ሰው ቢሸጥ እንደ ገና ይቤዠው ዘንድ አይቻለውም። 21እርሻው ግን በኢዮቤልዩ ዓመት ሲወጣ ለእግዚአብሔር የተቀደሰ እርሻ ይሆናል፤ ርስቱም ለካህኑ ይሆናል። 22ከርስቱ እርሻ ያልሆነውን የገዛውን እርሻ ለእግዚአብሔር ቢሳል፥ 23ካህኑ እስከ ኢዮቤልዩ ዓመት ድረስ የግምቱን ዋጋ ይቈጥርለታል፤ በዚያም ቀን ግምቱን እንደ ተቀደሰ ነገር ለእግዚአብሔር ይሰጣል። 24በኢዮቤልዩ ዓመት እርሻው የምድሪቱ ባለ ርስት ወደ ነበረው ወደ ሸጠው ሰው ይመለሳል፤ የራሱ ወሰን ምድር ነውና።#በግእዙ “እስመ ደወለ ዚኣሁ ውእቱ ወምድሩ” የሚል ይገኛል። 25ግምቱም ሁሉ እንደ መቅደሱ ሚዛን ይሆናል፤ አንዱ ዲድርክም ሃያ አቦሊ ይሆናል።
26“ከእንስሳህ የሚወለድ በኵር ሁሉ ለእግዚአብሔር ነው፤ ማንም ይለውጠው ዘንድ አይቻለውም፤ በሬ ቢሆን ወይም በግ ለእግዚአብሔር ነው። 27የረከሰም እንስሳ ቢሆን እንደ ግምቱ ይቤዠው፤ በእርሱም የዋጋውን አምስተኛ እጅ ይጨምርበታል፤ ባይቤዥም እንደ ግምቱ ይሸጣል።
28“ለእግዚአብሔርም የተለየ እርም የሆነ ነገር ሁሉ፥ ሰው ቢሆን ወይም እንስሳ ወይም የርስቱ እርሻ ቢሆን፥ አይሸጥም፤ አይቤዥም፤ እርም የሆነ ነገር ሁሉ ለእግዚአብሔር ቅዱሰ ቅዱሳን ነው። 29ከሰዎችም መባ ሆኖ የቀረበ ሁሉ እስኪሞት ድረስ አይቤዥም።#ግሪክ ሰባ. ሊ. “አይቤዥም ፈጽሞ ይገደል” የሚል ይጨምራል።
30“የምድርም ዐሥራት፥ ወይም የምድር ዘር፥ ወይም የዛፍ ፍሬ ቢሆን፥ የእግዚአብሔር ነው፤ ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ነው። 31ሰውም ዐሥራቱን ሊቤዥ ቢወድድ፥ አምስተኛ እጅ ይጨመርበታል። 32ከበሬም ሁሉ ከዐሥር አንድ፥ ከበግም ሁሉ ከዐሥር አንድ፥ ከእረኛውም በትር በታች ከሚያልፍ ሁሉ ከዐሥር አንድ ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ይሆናል። 33መልካሙን በክፉ፥ ክፉውንም በመልካም አይለውጥ፤ ቢለውጠውም እርሱና ልዋጩ የተቀደሱ ይሆናሉ፤ አይቤዠውም።”
34እግዚአብሔር በሲና ተራራ ላይ ለእስራኤል ልጆች ያስተምራቸው ዘንድ ሙሴን ያዘዘው ትእዛዛት እነዚህ ናቸው።
Currently Selected:
ኦሪት ዘሌዋውያን 27: አማ2000
ማድመቅ
ያጋሩ
ኮፒ

ያደመቋቸው ምንባቦች በሁሉም መሣሪያዎችዎ ላይ እንዲቀመጡ ይፈልጋሉ? ይመዝገቡ ወይም ይግቡ