ኦሪት ዘሌዋውያን 15
15
ከሰውነቱ ፈሳሽ ስለሚፈስሰው ሰው የመንጻት ሕግ
1እግዚአብሔርም ሙሴንና አሮንን እንዲህ ብሎ ተናገራቸው፥ 2“ለእስራኤል ልጆች እንዲህ ብላችሁ ንገሩአቸው፦ ከሰውነቱ ዘር የሚፈስሰው ሰው ቢኖር ስለሚፈስሰው ነገር ርኩስ ነው። 3ከሰውነቱ ፈሳሽ ለሚፈስሰው ሰው የርኵሰቱ ሕግ ይህ ነው፤ ፈሳሽ የሚፈስሰው ሰው ፈሳሹ እየፈሰሰው በሚኖርበት ጊዜ ሁሉ ርኩስ ነው፤ ፈሳሹ ያረክሰዋል። 4ፈሳሽ ነገር ያለበት ሰው የሚተኛበት መኝታ ሁሉ ርኩስ ነው፤ የሚቀመጥበትም ነገር ሁሉ ርኩስ ነው። 5መኝታውንም የሚነካ ሰው ሁሉ ልብሱን ይጠብ፤ በውኃም ሰውነቱን ይታጠብ፤ እስከ ማታም ድረስ ርኩስ ነው። 6ፈሳሽ ነገር ያለበት ሰው በተቀመጠበት ነገር ላይ የሚቀመጥበት ሰው ልብሱን ይጠብ፤ በውኃም ይታጠብ፤ እስከ ማታም ድረስ ርኩስ ነው። 7ፈሳሽ ነገር ያለበትን የሰውን ሥጋ የሚነካ ልብሱን ይጠብ፤ በውኃም ይታጠብ፤ እስከ ማታም ድረስ ርኩስ ነው። 8ፈሳሽ ነገር ያለበት ሰው በንጹሕ ሰው ላይ ቢተፋ ልብሱን ይጠብ፤ በውኃም ይታጠብ፤ እስከ ማታም ድረስ ርኩስ ነው። 9ፈሳሽ ነገር ያለበት ሰው የተቀመጠበት ኮርቻ ሁሉ ርኩስ ነው። 10ከበታቹም ያለውን ነገር የሚነካ ሁሉ እስከ ማታ ድረስ ርኩስ ነው፤ እነዚህንም ነገሮች የሚያነሣ ሁሉ ልብሱን ይጠብ፤ በውኃም ይታጠብ፤ እስከ ማታም ድረስ ርኩስ ነው። 11ፈሳሽ ነገር ያለበት ሰው እጁን በውኃ ሳይታጠብ የሚነካው ሁሉ ልብሶቹን ይጠብ፤ በውኃም ይታጠብ፤ እስከ ማታም ርኩስ ነው። 12ፈሳሽ ነገር ያለበት ሰው የሚነካውን የሸክላ ዕቃ ይስበሩት፤ የዕንጨቱንም ዕቃ ሁሉ በውኃ ይጠቡት፤ ንጹሕም ይሆናል።
13“ፈሳሽ ነገር ያለበት ሰው ከፈሳሹ ነገር ሲነጻ ስለ መንጻቱ ሰባት ቀን ይቈጥራል፤ ልብሶቹንም ያጥባል፤ ገላውንም በምንጭ ውኃ ይታጠባል፤ ንጹሕም ይሆናል። 14በስምንተኛውም ቀን ሁለት ዋኖሶች ወይም ሁለት የርግብ ግልገሎች ይዞ ወደ ምስክሩ ድንኳን ደጃፍ በእግዚአብሔር ፊት ያመጣል፤ ለካህኑም ይሰጠዋል። 15ካህኑም አንዲቱን ለኀጢአት መሥዋዕት፥ አንዲቱንም ለሚቃጠል መሥዋዕት ያቀርባል፤ ካህኑም በእግዚአብሔር ፊት ስለ ፈሳሹ ነገር ሁሉ ያስተሰርይለታል።
16“ማንም ሰው ዘር ከእርሱ ቢወጣ፥#ግእዙ “እመቦ ብእሲ ዘሰከበ ምስለ ብእሲት” ይላል። ገላውን ሁሉ በውኃ ይታጠባል፤ እስከ ማታም ርኩስ ነው። 17ዘር የነካው ልብስ ሁሉ፥ ቍርበትም ሁሉ በውኃ ይታጠባል፤ እስከ ማታም ድረስ ርኩስ ነው። 18ሴት ፈሳሽ ከአለበት ወንድ ጋር ብትገናኝ ሁለቱም በውኃ ይታጠባሉ፤ እስከ ማታም ድረስ ርኩሳን ናቸው።
19“ሴት ፈሳሽ ነገር ቢኖርባት፥ በሥጋዋም ያለው ፈሳሽ ነገር ደም ቢሆን፥ በግዳጅዋ ሰባት ቀን ትቀመጣለች፤ የሚነካትም ሁሉ እስከ ማታ ድረስ ርኩስ ነው። 20በግዳጅም ሳለች የምትተኛበት ነገር ሁሉ ርኩስ ነው፤ የምትቀመጥበትም ነገር ሁሉ ርኩስ ነው። 21መኝታዋንም የሚነካ ሁሉ ልብሶቹን ያጥባል፤ በውኃም ሰውነቱን ይታጠባል፤ እስከ ማታም ድረስ ርኩስ ነው። 22የምትቀመጥበትንም ነገር ሁሉ የሚነካ ሁሉ ልብሶቹን ያጥባል፤ በውኃም ሰውነቱን ይታጠባል፤ እስከ ማታም ርኩስ ነው። 23በመኝታዋም ላይ ወይም በምትቀመጥበት ነገር ላይ ቢሆን ሲነካው እስከ ማታ ድረስ ርኩስ ነው። 24ማንም ከእርስዋ ጋር ቢተኛ፥ ግዳጅዋም ቢነካው፥ ሰባት ቀን ርኩስ ነው፤ የሚተኛበትም መኝታ ሁሉ ርኩስ ነው።
25“ሴትም ከግዳጅዋ ቀን ሌላ ደምዋ ብዙ ቀን ቢፈስስ፥ ወይም ደምዋ ከግዳጅዋ ወራት በኋላ ቢፈስስ፥ በግዳጅዋ ወራት እንደ ሆነች እንዲሁ በፈሳሽዋ ርኩስነት ወራት ትሆናለች፤ ርኵስት ናት። 26ደምዋም በሚፈስስበት ወራት ሁሉ የምትተኛበት መኝታ ሁሉ በግዳጅዋ ጊዜ እንደ ነበረው መኝታ ያለ ይሆንባታል፤ የምትቀመጥበት ነገር ሁሉ እንደ ግዳጅዋ ርኩስነት ርኩስ ነው። 27እነዚህንም ነገሮች የሚነካ ሁሉ ርኩስ ነው፤ ልብሱንም ያጥባል፤ በውኃም ይታጠባል፤ እስከ ማታም ርኩስ ነው። 28ከፈሳሽዋም ብትነጻ ሰባት ቀን ትቈጥራለች፤ ከዚያም በኋላ ንጽሕት ትሆናለች። 29በስምንተኛውም ቀን ሁለት ዋኖሶች ወይም ሁለት የርግብ ግልገሎች ይዛ ወደ ካህኑ ወደ ምስክሩ ድንኳን ደጃፍ ታመጣቸዋለች። 30ካህኑም አንዲቱን ለኀጢአት መሥዋዕት፥ አንዲቱንም ለሚቃጠል መሥዋዕት ያቀርባል፤ ካህኑም ስለ ፈሳሽዋ ርኩስነት በእግዚአብሔር ፊት ያስተሰርይላታል።
31“እንዲሁም በእነርሱ መካከል ያለችውን ድንኳኔን ባረከሱ ጊዜ፥ በርኩስነታቸው እንዳይሞቱ የእስራኤልን ልጆች ከርኩስነታቸው አንጹአቸው።
32“ፈሳሽ ነገር ላለበት ሰው፥ ይረክስም ዘንድ ዘሩ ለሚወጣበት ሰው፥ 33በግዳጅዋም ደም ለሚፈስሳት፥ ፈሳሽም ነገር ላለባቸው ለወንድም ለሴትም፥ ከረከሰችም ሴት ጋር ለሚተኛ ሰው ሕጉ ይህ ነው።”
Currently Selected:
ኦሪት ዘሌዋውያን 15: አማ2000
ማድመቅ
ያጋሩ
ኮፒ

ያደመቋቸው ምንባቦች በሁሉም መሣሪያዎችዎ ላይ እንዲቀመጡ ይፈልጋሉ? ይመዝገቡ ወይም ይግቡ