የሐ​ዋ​ር​ያት ሥራ 16:25-40

የሐ​ዋ​ር​ያት ሥራ 16:25-40 አማ2000

በመ​ን​ፈቀ ሌሊ​ትም ጳው​ሎ​ስና ሲላስ ጸለዩ፤ እግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ር​ንም በዜማ አመ​ሰ​ገ​ኑት፤ እስ​ረ​ኞ​ቹም ይሰ​ሙ​አ​ቸው ነበር። ድን​ገ​ትም ታላቅ ንው​ጽ​ው​ጽታ ሆነ፤ የወ​ህኒ ቤቱ መሠ​ረ​ትም ተና​ወጠ፤ በሮ​ችም ሁሉ ያን​ጊዜ ተከ​ፈቱ፤ የሁ​ሉም እግር ብረ​ቶ​ቻ​ቸው እየ​ወ​ለቁ ወደቁ። የወ​ህኒ ቤቱ ጠባ​ቂም ከእ​ን​ቅ​ልፉ በነቃ ጊዜ በሮች ሁሉ ተከ​ፍ​ተው አየ፤ ሰይ​ፉ​ንም መዝዞ ራሱን ሊገ​ድል ወደደ፤ እስ​ረ​ኞቹ ያመ​ለ​ጡት መስ​ሎት ነበ​ርና። ጳው​ሎ​ስም፥ “በራ​ስህ ክፉ ነገር አታ​ድ​ርግ፤ ሁላ​ች​ንም ከዚህ አለን” ብሎ በታ​ላቅ ቃል ጮኸ። መብ​ራት አም​ጥ​ቶም እየ​ተ​ን​ቀ​ጠ​ቀጠ ወደ ውስጥ ሄደና ለጳ​ው​ሎ​ስና ለሲ​ላስ ወድቆ ሰገደ። ወደ ውጭም አው​ጥቶ “ጌቶች፥ እድን ዘንድ ምን ላድ​ርግ?” አላ​ቸው። እነ​ር​ሱም፥ “በጌ​ታ​ችን በኢ​የ​ሱስ ክር​ስ​ቶስ እመን፤ አን​ተና ቤተ ሰብ​ህም ሁሉ ትድ​ና​ላ​ችሁ” አሉት። የእ​ግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ር​ንም ቃል ለእ​ር​ሱና በቤቱ ላሉት ሁሉ ነገ​ሩ​አ​ቸው። ወዲ​ያ​ው​ኑም በሌ​ሊት ወስዶ ቍስ​ላ​ቸ​ውን አጠ​በ​ላ​ቸው፤ እር​ሱም በዚ​ያው ጊዜ ከቤተ ሰቡ ሁሉ ጋር ተጠ​መቀ። ወደ ቤቱም አግ​ብቶ ማዕድ አቀ​ረ​በ​ላ​ቸው፤ በጌ​ታ​ችን ስለ አመ​ነም እርሱ ከቤተ ሰቡ ጋር ደስ አለው። በነጋ ጊዜም፥ ገዢ​ዎቹ፥ “እነ​ዚ​ያን ሰዎች ፈት​ታ​ችሁ ልቀ​ቋ​ቸው” ብለው ብላ​ቴ​ኖ​ቻ​ቸ​ውን ላኩ። የወ​ህኒ ቤቱ ጠባ​ቂም በሰማ ጊዜ ሄዶ ገዢ​ዎቹ “ይፈቱ” ብለው እንደ ላኩ ይህን ነገር ለጳ​ው​ሎ​ስና ለሲ​ላስ ነገ​ራ​ቸው፤ “አሁ​ንም ውጡና በሰ​ላም ሂዱ” አላ​ቸው። ጳው​ሎስ ግን፥ “እኛ የሮም ሰዎች ስን​ሆን፥ ያለ ፍርድ በአ​ደ​ባ​ባይ ገረ​ፉን፤ አሰ​ሩ​ንም፤ አሁ​ንም በስ​ውር ሊያ​ወ​ጡን ይሻሉ፤ አይ​ሆ​ንም፥ ራሳ​ቸው መጥ​ተው ያው​ጡን” አላ​ቸው። ብላ​ቴ​ኖ​ቻ​ቸ​ውም ሄደው ይህ​ንን ነገር ለገ​ዢ​ዎቹ ነገ​ሩ​አ​ቸው፤ የሮም ሰዎች መሆ​ና​ቸ​ው​ንም ሰም​ተው ደነ​ገጡ። መጥ​ተ​ውም ከከ​ተ​ማ​ቸው እን​ዲ​ወጡ ማለ​ዱ​አ​ቸው። ከወ​ኅኒ ቤቱም ከወጡ በኋላ ወደ ልድያ ቤት ገብ​ተው ወን​ድ​ሞ​ችን አገኙ፤ አጽ​ና​ን​ተ​ዋ​ቸ​ውም ሔዱ።