መዝሙረ ዳዊት 55:1-23

መዝሙረ ዳዊት 55:1-23 መቅካእኤ

አቤቱ፥ ጸሎቴን አድምጥ፥ ልመናዬንም ቸል አትበል። ተመልከተኝ መልስም ስጠኝ፥ በኀዘኔ ተቅበዘበዝሁ ተናወጥሁም፥ ከጠላት ድምፅ ከዓመፀኛም ግፍ የተነሣ፥ ዓመፃን በላዬ ጥለውብኛልና፥ በቁጣም ጠልተውኛልና። ልቤ በላዬ ተናወጠብኝ፥ የሞት ድንጋጤም ወደቀብኝ። ፍርሃትና እንቅጥቅጥ መጡብኝ፥ መዘግነን ሸፈነኝ። በርሬ ዐርፍ ዘንድ እንደ ርግብ ክንፍን ማን በሰጠኝ! እነሆ፥ ኰብልዬ በራቅሁ በምድረ በዳም በተቀመጥሁ፥ ከዐውሎና ከብርቱ ንፋስ ሸሽቼ በፈጠንሁ አልሁ። አቤቱ፥ ግፍንና ጠብን በከተማ ውስጥ አይቼአለሁና አስጥማቸው አንደበታቸውንም ቁረጥ። በቀንና በሌሊት በቅጥርዋ ይከብቡአታል፥ በደልና ሁከት በመካከልዋ ነው፥ በውስጧ ጥፋት አለ፤ ተንኰልና ሽንገላ ከአደባባይዋ አይርቁም። ጠላትስ ቢሰድበኝ፥ በታገሥሁ ነበር፥ የሚጠላኝም ራሱን በላዬ ከፍ ከፍ ቢያደርግ፥ ከእርሱ በተሸሸግሁ ነበር። አንተ ግን፥ እኩያዬ ሰው፥ ባልንጀራዬና የልቤ ወዳጅ፥ መብልን ከእኔ ጋር በአንድነት ያጣፈጥህ፥ በአንድ ልብ በእግዚአብሔር ቤት ተራመድን። ሞት ይምጣባቸው፥ በሕይወት ሳሉ ወደ ሲኦል ይውረዱ፥ ክፋት በማደሪያቸውና በመካከላቸው ነውና። እኔ ግን ወደ እግዚአብሔር ጮኽሁ፥ ጌታም ያድነኛል። በማታና በጥዋት በቀትርም አቤቱታ አቀርባለሁ እጮኽማለሁ፥ ቃሌንም ይሰማኛል። በእኔ ላይ ብዙ ነበሩና ከተቃጣብኝ ጦርነት ነፍሴን በሰላም ያድናታል። አይለወጡምና፥ እግዚአብሔርንም አልፈሩትምና ከጥንት ጀምሮ የነበረ እግዚአብሔር ሰምቶ ያጐሰቁላቸዋል። ወዳጄ ከእርሱ ጋር ሰላም በነበሩት ላይ እጁን ዘረጋ፥ ኪዳኑንም አፈረሰ። አፉ ከቅቤ ይልቅ ለዘበ፥ በልቡ ውስጥ ግን ጦርነት ነበረ፥ ቃሎቹም ከዘይት ይልቅ ለሰለሱ፥ ነገር ግን እንደ ተመዘዘ ሰይፍ ናቸው። ሸክምህን በጌታ ላይ ጣል፥ እርሱም ይደግፍሃል፥ ለጻድቁም ለዘለዓለም ሁከትን አይሰጠውም።