መጽሐፈ ምሳሌ 5:1-14

መጽሐፈ ምሳሌ 5:1-14 አማ05

ልጄ ሆይ! እኔ ወደምነግርህ ጥበብና ማስተዋል አተኲረህ አድምጥ። ይህን ብታደርግ አስተዋይነት ይኖርሃል፤ ንግግርህም ዕውቀት እንዳለህ ይገልጣል፤ የአመንዝራ ሴት ከንፈር የማር ወለላ የሚያንጠባጥብ ይመስላል፤ ንግግርዋም ከዘይት ይልቅ የለዘበ ነው። በመጨረሻ ግን እርስዋ እንደ እሬት የመረረችና ሁለት አፍ እንዳለው ስለታም ሰይፍ የምትቈርጥ ነች። መንገዶችዋ ወደ ሞት የሚያደርሱ ናቸው፤ እርምጃዎችዋም ወደ ሲኦል ይመራሉ። ወደ ሕይወት በሚመራው መንገድ አትሄድም፤ እንዲሁ ትባዝናለች፤ መባዘንዋን ግን አታውቀውም። ልጄ ሆይ! አድምጠኝ፤ እኔም ከምነግርህ ትምህርት አትራቅ። እንደዚህች ካለችው ሴት ራቅ፤ ወደ ቤትዋ ደጃፍ እንኳ አትቅረብ። አለበለዚያ፥ አንተ የነበረህን ክብር ሌሎች ይወስዱታል፤ ገና በወጣትነትህ በጨካኞች ሰዎች እጅ ትገደላለህ፤ ሀብትህን ሁሉ ባዕዳን ሰዎች ይወስዱታል፤ የደከምክበትም ንብረት ለሌላ ሰው ይሆናል። ሁለንተናህ ተበልቶ ከማለቁ የተነሣ በሞት ጣዕር ተይዘሃል፥ እንዲህም ትላለህ፦ “የማልማረውና የሰውን ተግሣጽ የማልቀበለው ከቶ ለምንድን ነው! አስተማሪዎቼ የሚሉትን መስማት አልፈለግሁም፤ ምክራቸውንም አልተቀበልሁም። ስለዚህ ሕዝብ በተሰበሰበበት አደባባይ መካከል ወደ ጥፋት ለመድረስ ተቃረብኩ።”