የYouVersion አርማ
የፍለጋ አዶ

ነህምያ 2:1-20

ነህምያ 2:1-20 NASV

በንጉሡ በአርጤክስስ ዘመነ መንግሥት በሃያኛው ዓመት ኒሳን ተብሎ በሚጠራው ወር የወይን ጠጅ በመጣለት ጊዜ፣ የወይን ጠጁን አንሥቼ ለንጉሡ ሰጠሁት። ቀድሞ በፊቱ ዐዝኜ አላውቅም ነበር፤ ስለዚህ ንጉሡ፣ “ሳትታመም ፊትህ ለምን እንዲህ ዐዘነ? መቼም ይህ የልብ ሐዘን እንጂ ሌላ አይደለም” አለኝ። እኔም በጣም ፈርቼ ነበር፤ ለንጉሡም “ንጉሡ ለዘላለም ይኑር፤ አባቶቼ የተቀበሩባት ከተማ ስትፈርስ፣ በሮቿም በእሳት ሲቃጠሉ ለምን ፊቴ አይዘን?” አልሁት። ንጉሡም፣ “ታዲያ ምን ትፈልጋለህ?” አለኝ። ከዚያም ወደ ሰማይ አምላክ ጸለይሁ፤ ለንጉሡም፣ “ንጉሡን ደስ የሚያሠኘው ቢሆንና ባሪያህ በፊትህ ሞገስ ቢያገኝ፣ እንደ ገና እንድሠራት አባቶቼ ወደ ተቀበሩባት ወደ ይሁዳ ከተማ እንድሄድ ይፈቀድልኝ” አልሁት። ከዚያም ንጉሡ አጠገቡ ከተቀመጠችው ንግሥት ጋራ በመሆን፣ “ጕዞህ ምን ያህል ቀን ይፈጃል? መቼስ ትመለሳለህ?” ሲል ጠየቀኝ። ንጉሡም እኔን ለመስደድ ደስ አለው፤ እኔም ጊዜውን ወሰንሁ። ደግሞም እንዲህ አልሁት፤ “ንጉሡን ደስ የሚያሠኘው ቢሆን፣ ይሁዳ እስክደርስ ድረስ በደኅና እንዲያሳልፉኝ ከኤፍራጥስ ማዶ ላሉት አገረ ገዦች ደብዳቤ ይሰጠኝ፤ እንዲሁም ለንጉሡ ደን ጠባቂ ለአሳፍ፣ በቤተ መቅደሱ አጠገብ ላለው ግንብ በሮች፣ ለከተማዪቱ ቅጥርና እኔም ለምገባበት ቤት ሠረገላ የሚሆን ዕንጨት እንዲሰጠኝ ደብዳቤ ይጻፍልኝ፤” መልካሚቱ የአምላኬ እጅ በእኔ ላይ ነበረችና ንጉሡም ፈቀደልኝ። ስለዚህ በኤፍራጥስ ማዶ ወደሚገኙት አገረ ገዦች ሄጄ የንጉሡን ደብዳቤዎች ሰጠኋቸው፤ ንጉሡም የጦር አለቆችና ፈረሰኞች ዐብረውኝ እንዲሄዱ አድርጎ ነበር። ሖሮናዊው ሰንባላጥና አሞናዊው ሹም ጦቢያ ይህን በሰሙ ጊዜ፣ ስለ እስራኤላውያን ደኅንነት የሚቈረቈር ሰው በመምጣቱ እጅግ ተበሳጩ። እኔም ወደ ኢየሩሳሌም ሄድሁ፤ በዚያም ሦስት ቀን ከቈየሁ በኋላ፣ ከጥቂት ሰዎች ጋራ በሌሊት ወጣሁ። ለኢየሩሳሌም አደርገው ዘንድ አምላኬ በልቤ ያኖረውን ነገር ለማንም አልነገርሁም፤ ከተቀመጥሁበት እንስሳ በቀር ከእኔ ጋራ ሌሎች እንስሳት አልነበሩም። በሌሊትም ወጥቼ በሸለቆው በር በኩል አድርጌ ወደ ዘንዶው የውሃ ጕድጓድና ወደ ቈሻሻ መድፊያው በር ሄድሁ፤ የፈረሱትንም የኢየሩሳሌምን ቅጥሮችና በእሳት የወደሙትን በሮች ተመለከትሁ። ከዚያም ወደ ውሃ ምንጭ በርና ወደ ንጉሡ ኵሬ ሄድሁ፤ ይሁን እንጂ የተቀመጥሁበትን እንስሳ ማሳለፍ የሚያስችል በቂ ቦታ አልነበረም። ስለዚህ ቅጥሩን እየተመለከትሁ ሌሊቱን ሸለቆውን ዐልፌ ወደ ላይ ወጣሁ፤ በመጨረሻም ተመልሼ በሸለቆው በር በኩል ገባሁ። ለአይሁድ ወይም ለካህናቱ ወይም ለመኳንንቱ ወይም ለሹማምቱ ወይም ሥራውን ለሚሠሩት ሰዎች ገና ምንም የተናገርሁት ነገር ስላልነበረ፣ ወዴት እንደ ሄድሁ ወይም ምን እንዳደረግሁ ሹማምቱ አላወቁም። ከዚያም፣ “ያለንበትን ችግር ይኸው ታያላችሁ፤ ኢየሩሳሌም ፈርሳለች፤ በሮቿም በእሳት ጋይተዋል፤ አሁንም ኑና የኢየሩሳሌምን ቅጥር እንደ ገና እንሥራ፤ ከእንግዲህስ መሣለቂያ አንሆንም” አልኋቸው። እንዲሁም መልካሚቱ የአምላኬ እጅ በእኔ ላይ እንደ ነበረችና ንጉሡም ምን እንዳለኝ ነገርኋቸው። እነርሱም፣ “እንደ ገና መሥራቱን እንጀምር!” ካሉ በኋላ ይህን መልካም ሥራ ጀመሩ። ነገር ግን ሖሮናዊው ሰንባላጥ፣ አሞናዊው ሹም ጦቢያና ዐረባዊው ጌሳም ይህን ሲሰሙ አፌዙብን፤ አንቋሸሹንም፤ እንዲሁም፣ “የምታደርጉት ይህ ምንድን ነው? በንጉሡ ላይ ልታምፁ ትፈልጋላችሁን?” አሉ። እኔም፣ “የሰማይ አምላክ ያከናውንልናል፤ እኛ ባሪያዎቹ እንደ ገና ሥራውን እንጀምራለን፤ እናንተ ግን በኢየሩሳሌም ድርሻ ወይም ይገባናል የምትሉት ወይም የታሪክ መታሰቢያ የላችሁም” ስል መለስሁላቸው።