YouVersion Logo
Search Icon

የዮሐንስ ወንጌል መግቢያ

መግቢያ
የዮሐንስ ወንጌል ኢየሱስን የሚያቀርበው ሥጋ ለብሶ በሰዎች መካከል የተገኘ ሕያው የእግዚአብሔር ቃል መሆኑን ለመግለጥ ነው፤ መጽሐፉ ራሱ እንደሚገልጠው ይህ ወንጌል የተጻፈው አንባቢዎች ኢየሱስ አዳኝ ሆኖ ይመጣል የተባለው የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን እንዲያምኑና በእርሱም በማመናቸው ምክንያት የዘለዓለም ሕይወት እንደሚኖራቸው እንዲረዱ ነው (20፥31)
የወንጌሉ መጀመሪያ ክፍል ዘለዓለማዊው የእግዚአብሔር ቃልና ኢየሱስ አንድ መሆናቸውን በመግቢያ መልክ ካቀረበ በኋላ ኢየሱስ አዳኝ ሆኖ ይመጣል የተባለው የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን የሚያሳዩትን ልዩ ልዩ ተአምራት ያቀርባል፤ ከዚያም ከእነዚህ ተአምራት ምን ውጤት እንደ ተገኘ የሚያስረዱት ታሪኮች ይከተላሉ፤ ይህኛው ክፍል የሚተርከው አንዳንድ ሰዎች በኢየሱስ አምነው የእርሱ ተከታዮች ስለ መሆናቸው፥ ሌሎች ደግሞ እንዴት እንደ ተቃወሙትና በእርሱ አናምንም እንዳሉ ነው፤ በምዕራፍ 13-17 ኢየሱስ በተያዘበት ምሽት ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ምን ያኽል የጠበቀ ግንኙነት እንደ ነበረውና በስቅለቱም ዋዜማ የመዘጋጀትና የመጽናናት ቃል እንዳሰማቸው ይናገራሉ። የመጨረሻዎቹ ምዕራፎች ስለ ኢየሱስ መያዝና ለፍርድ መቅረብ፥ ስለ ስቅለቱና ትንሣኤው፥ እንዲሁም ከትንሣኤው በኋላ ለደቀ መዛሙርቱ ስለ መገለጡ የሚያወሱ ናቸው።
ዮሐንስ በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት የሚገኘውን ዘለዓለማዊ ሕይወት ጐላ አድርጎ የሚያሳየው ይህ ጸጋ ከአሁኑ ጀምሮ ኢየሱስን እንደ መንገድ፥ እንደ እውነት፥ እንደ ሕይወትም አድርገው ለሚቀበሉት ነው። የዮሐንስን ወንጌል ልዩ የሚያደርገው መንፈሳዊ እውነቶችን ለማስረዳት የተለመዱና በዕለታዊ ኑሮ የምንጠቀምባቸውን፥ ማለትም እንደ ውሃ፥ እንጀራ፥ ብርሃን፥ እረኛ፥ በጎች፥ የወይን ተክልና የወይን ፍሬ የመሳሰሉ ነገሮች በምሳሌ መጠቀሙ ነው።
አጠቃላይ የመጽሐፉ ይዘት
መቅድም 1፥1-18
ዮሐንስ መጥምቁና የኢየሱስ የመጀመሪያዎቹ ደቀ መዛሙርት 1፥19-51
ኢየሱስ አገልግሎቱን መጀመሩ 2፥1—12፥50
በኢየሩሳሌምና በአካባቢዋ የአገልግሎቱ የመጨረሻዎቹ ቀኖች 13፥1—19፥42
የጌታ ትንሣኤና መገለጡ 20፥1-31
ማጠቃለያ፦ በገሊላ እንደገና ለደቀ መዛሙርቱ መገለጡ 21፥1-25

Highlight

Share

Copy

None

Want to have your highlights saved across all your devices? Sign up or sign in