YouVersion Logo
Search Icon

የዮሐንስ ወንጌል 1

1
የሕይወት ቃል
1ቃል በመጀመሪያ ነበረ፤ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፤ ይህም ቃል እግዚአብሔር ነበረ። 2እርሱ በመጀመሪያ በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ። 3ሁሉ ነገር በእርሱ ተፈጠረ፤ ከተፈጠረው ሁሉ፥ አንድም ነገር ያለ እርሱ የተፈጠረ የለም። 4በእርሱ ሕይወት ነበረ፤ ይህም ሕይወት የሰዎች ብርሃን ነበረ። 5ብርሃን በጨለማ ያበራል፤ ጨለማም ብርሃንን አያሸንፈውም።
6ከእግዚአብሔር የተላከ ዮሐንስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፤ #ማቴ. 3፥1፤ ማር. 1፥4፤ ሉቃ. 3፥1-2። 7በእርሱ ምስክርነት ሰው ሁሉ እንዲያምን ስለ ብርሃን ምስክር ሆኖ መጣ። 8እርሱ ስለ ብርሃን ሊመሰክር መጣ እንጂ እርሱ ራሱ ብርሃን አልነበረም። 9ለሰው ሁሉ የሚያበራው እውነተኛው ብርሃን ወደ ዓለም እየመጣ ነበር።
10እርሱም በዓለም ነበረ፤ ዓለምም የተፈጠረው በእርሱ ነው፤ ዓለም ግን አላወቀውም። 11ወደ ወገኖቹ መጣ ወገኖቹ ግን አልተቀበሉትም። 12ይሁን እንጂ ለተቀበሉትና በስሙ ላመኑ ሁሉ የእግዚአብሔር ልጆች የመሆንን መብት ሰጣቸው። 13እነርሱም ከእግዚአብሔር ተወለዱ እንጂ ከሰው ዘር፥ ማለትም ከሥጋ ፈቃድ ወይም ከሰው ፈቃድ አልተወለዱም።
14ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በመካከላችን ኖረ፤ የአባቱ አንድያ ልጅ በአባቱ ዘንድ እንዳለው ያለውን ክብሩን አይተናል።
15ዮሐንስም “ ‘ያ ከእኔ በኋላ የሚመጣው ከእኔ በፊት ስለነበረ ከእኔ እጅግ ይበልጣል’ ብዬ የነገርኳችሁ እነሆ፥ ይህ ነው” እያለ መሰከረ።
16ከእርሱ የጸጋ ሙላት እኛ ሁላችን በጸጋ ላይ ጸጋን ተቀብለናል። 17ሕግ በሙሴ በኩል ተሰጠ፤ ጸጋና እውነት ግን በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል መጣ። 18እግዚአብሔርን ያየው ከቶ ማንም የለም፤ ይሁን እንጂ በእግዚአብሔር አብ ዘንድ ያለው አንድያ ልጁ ብቻ ገለጠው።
የመጥምቁ ዮሐንስ ምስክርነት
(ማቴ. 3፥1-12ማር. 1፥1-8ሉቃ. 3፥1-18)
19የአይሁድ ባለሥልጣኖች ከኢየሩሳሌም ካህናትንና ሌዋውያንን ወደ ዮሐንስ ልከው፦ “አንተ ማን ነህ?” ብለው ባስጠየቁት ጊዜ የሰጠው ምስክርነት የሚከተለው ነው፤
20እርሱ “እኔ መሲሕ አይደለሁም” ሲል መሰከረ እንጂ አልካደም።
21እነርሱም “ታዲያ አንተ ማን ነህ? ኤልያስ ነህን?” ሲሉ ጠየቁት። #ዘዳ. 18፥15፤18፤ ሚል. 4፥5።
እርሱም “አይደለሁም” ሲል መለሰላቸው።
እነርሱም “ይመጣል የተባለው ነቢይ ነህን?” አሉት።
እርሱም “አይደለሁም” አለ።
22እነርሱም “ታዲያ አንተ ማን ነህ? ለላኩን ሰዎች መልሱን እንድንነግር ስለ ራስህ ምን ትላለህ?” አሉት። 23እርሱም “ነቢዩ ኢሳይያስ እንደ ተናገረው
እኔ ‘የጌታን መንገድ አቅኑ’ እያለ
በበረሓ የሚጮኽ ሰው ድምፅ ነኝ” አለ። #ኢሳ. 40፥3።
24ሰዎቹ የተላኩት ከፈሪሳውያን ነበረ፤ 25ስለዚህ “አንተ መሲሕ ወይም ኤልያስ ወይም ይመጣል የተባለው ነቢይ ካልሆንክ ታዲያ፥ ስለምን ታጠምቃለህ?” ሲሉ ጠየቁት።
26ዮሐንስም እንዲህ ሲል መለሰላቸው፦ “እኔ የማጠምቀው በውሃ ነው፤ ነገር ግን እናንተ የማታውቁት በመካከላችሁ ቆሞአል። 27እርሱ ከእኔ በኋላ የሚመጣ ነው፤ እኔ የጫማውን ማሰሪያ ለመፍታት እንኳ የበቃሁ አይደለሁም።”
28ይህ የሆነው ዮሐንስ ያጠምቅ በነበረበት ከዮርዳኖስ ወንዝ ማዶ በምትገኘው በቢታንያ ከተማ ነው።
የእግዚአብሔር በግ
29በማግስቱ ዮሐንስ ኢየሱስን ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ እንዲህ አለ፦ “እነሆ፥ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ ይህ ነው! 30‘ያ ከእኔ በኋላ የሚመጣው ከእኔ በፊት ስለ ነበረ ከእኔ እጅግ ይበልጣል’ ያልኳችሁ ይህ ነው። 31እኔም ራሴ አላውቀውም ነበር፤ ነገር ግን እርሱ ለእስራኤል ሕዝብ እንዲገለጥ እኔ በውሃ እያጠመቅሁ መጣሁ።”
32ቀጥሎም ዮሐንስ እንዲህ ሲል መሰከረ፦ “መንፈስ ቅዱስ እንደ ርግብ ከሰማይ ሲወርድና በእርሱ ላይ ሲያርፍበት አየሁ፤ 33እኔ ራሴ አላውቀውም ነበር፤ ነገር ግን በውሃ እንዳጠምቅ የላከኝ፥ ‘መንፈስ ቅዱስ ሲወርድና በእርሱ ላይ ሲያርፍበት የምታየው በመንፈስ ቅዱስ የሚያጠምቅ እርሱ ነው’ ሲል ነግሮኛል። 34እኔም ይህን አይቼአለሁ፤ ስለዚህ እርሱ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን እመሰክራለሁ።”
የመጀመሪያዎቹ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት
35በማግስቱ ዮሐንስ ከሁለት ደቀ መዛሙርቱ ጋር እንደገና እዚያ ቆሞ ነበር፤ 36ዮሐንስ ኢየሱስን በዚያ ሲያልፍ አይቶ፥ “እነሆ፥ የእግዚአብሔር በግ!” አለ።
37ሁለቱ የዮሐንስ ደቀ መዛሙርት ዮሐንስ ይህን ሲል ሰምተው፥ ኢየሱስን ተከተሉት። 38ኢየሱስ መለስ ብሎ ሲከተሉት አየና “ምን ትፈልጋላችሁ?” አላቸው።
እነርሱም “ረቢ! የምትኖረው የት ነው?” አሉት። (ረቢ ማለት መምህር ማለት ነው)
39እርሱም “ኑና እዩ” አላቸው። ስለዚህ ሄዱና የት እንደሚኖር አዩ። በዚያን ቀን ከእርሱ ጋር አብረው ዋሉ፤ ጊዜው ወደ ዐሥር ሰዓት ገደማ ነበር።
40ዮሐንስ የተናገረውን ቃል ሰምተው ኢየሱስን ከተከተሉት ደቀ መዛሙርት አንዱ የስምዖን ጴጥሮስ ወንድም እንድርያስ ነበር። 41እንድርያስ በመጀመሪያ ወደ ወንድሙ ወደ ስምዖን ሄደና “መሲሕን አገኘነው!” አለው። (መሲሕ ማለት ክርስቶስ ማለት ነው።) 42ከዚህ በኋላ እንድርያስ ስምዖንን ወደ ኢየሱስ አመጣው።
ኢየሱስም ትኲር ብሎ ተመለከተውና “አንተ የዮና ልጅ ስምዖን ነህ፤ ከእንግዲህ ወዲህ ግን ኬፋ ትባላለህ” አለው። (ኬፋ ማለት ጴጥሮስ ወይም አለት ማለት ነው።)
ኢየሱስ ፊልጶስንና ናትናኤልን እንደ ጠራ
43በማግስቱ ኢየሱስ ወደ ገሊላ ለመሄድ ፈለገ፤ ፊልጶስንም አገኘውና “ተከተለኝ!” አለው። 44ፊልጶስ እንደ እንድርያስና እንደ ጴጥሮስ የቤተ ሳይዳ ከተማ ሰው ነበረ። 45ፊልጶስ ናትናኤልን አግኝቶ፥ “ሙሴ በሕግ መጽሐፍ፥ ነቢያትም በትንቢት መጻሕፍት ስለ እርሱ የጻፉለትን አገኘነው፤ እርሱም የዮሴፍ ልጅ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነው” አለው። 46ናትናኤል ግን፥ “ከናዝሬት መልካም ነገር ከቶ ሊገኝ ይችላልን?” አለው። ፊልጶስም “መጥተህ እይ!” አለው። 47ናትናኤል ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ ኢየሱስ “እነሆ! ተንኰል የሌለበት እውነተኛ የእስራኤል ሰው!” ሲል ስለ እርሱ ተናገረ። 48ናትናኤልም “የት ታውቀኛለህ?” አለው። ኢየሱስም “ፊልጶስ ሳይጠራህ በፊት ከበለስ ዛፍ ሥር ሆነህ አይቼሃለሁ” ሲል መለሰለት። 49በዚህ ጊዜ ናትናኤል፥ “መምህር ሆይ! አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ! አንተ የእስራኤል ንጉሥ ነህ!” አለ።
50ኢየሱስም እንዲህ አለ፦ “አንተ ያመንከው፥ ‘ከበለስ ዛፍ ሥር ሆነህ አይቼሃለሁ’ ስላልኩህ ነውን? ከዚህ የበለጡ ነገሮችን ገና ታያለህ። 51እውነት፥ እውነት እላችኋለሁ፦ ሰማይ ሲከፈት የእግዚአብሔር መላእክትም በሰው ልጅ ላይ ሲወጡና ሲወርዱ ታያላችሁ።” #ዘፍ. 28፥12።

Highlight

Share

Copy

None

Want to have your highlights saved across all your devices? Sign up or sign in