YouVersion Logo
Search Icon

ሰቈቃወ 4

4
א አሌፍ
# 4 ይህ ምዕራፍ፣ ጥቅሶቹ ተከታታይ ፊደላት ባሉት የዕብራይስጥ ሆህያት የሚጀምር ቃል ወይም ዐረፍተ ነገር ያለው ግጥም ነው። 1ወርቁ እንዴት ደበሰ!
ንጹሑስ ወርቅ እንዴት ተለወጠ!
የከበሩ ድንጋዮች፣
በየመንገዱ ዳር ተበታትነዋል።
ב ቤት
2እንደ ወርቅ ይቈጠሩ የነበሩ፣
የከበሩ የጽዮን ወንዶች ልጆች፣
የሸክላ ሠሪ እጅ እንደ ሠራው፣
እንዴት አሁን እንደ ሸክላ ዕቃ ሆኑ!
ג ጊሜል
3ቀበሮዎች እንኳን ግልገሎቻቸውን ለማጥባት፣
ጡታቸውን ይሰጣሉ፤
ሕዝቤ ግን በምድረ በዳ እንዳሉ ሰጎኖች፣
ጨካኞች ሆኑ።
ד ዳሌት
4ከውሃ ጥም የተነሣ፣
የሕፃናት ምላስ ከላንቃቸው ጋር ተጣበቀ፤
ልጆቹ ምግብ ለመኑ፤
ነገር ግን ማንም አልሰጣቸውም።
ה ሄ
5ምርጥ ምግብ ይበሉ የነበሩ፣
ተቸግረው በየመንገዱ ላይ ተንከራተቱ፤
ሐምራዊ ግምጃ ለብሰው ያደጉ፣
አሁን በዐመድ ክምር ላይ ተኙ።
ו ዋው
6በሕዝቤ ላይ የደረሰው ቅጣት፣
የማንም እጅ ሳይረዳት፣
በድንገት ከተገለበጠችው፣
ሰዶም ላይ ከደረሰው ቅጣት ይልቅ ታላቅ ነው።
ז ዛይን
7መሳፍንታቸው ከበረዶ ይልቅ ብሩህ፣
ከወተትም ይልቅ ነጭ ነበሩ፤
ሰውነታቸው ከቀይ ዕንየቀላ፣
መልካቸውም እንደ ሰንፌር#4፥7 ወይም ላፒስ ላዙሊ ነበር።
ח ኼት
8አሁን ግን ከጥላሸት ይልቅ ጠቍረዋል፤
በመንገድም የሚያውቃቸው የለም፤
ቈዳቸው ከዐጥንታቸው ጋር ተጣብቋል፤
እንደ ዕንጨትም ደርቀዋል።
ט ቴት
9በራብ ከሚሞቱት ይልቅ፣
በሰይፍ የተገደሉት ይሻላሉ፤
ምግብ በሜዳ ላይ ካለማግኘታቸው የተነሣ፣
በራብ ደርቀው ያልቃሉ።
י ዮድ
10ሕዝቤ ባለቀበት ጊዜ፣
ምግብ እንዲሆኗቸው፣
ርኅሩኆቹ ሴቶች በገዛ እጆቻቸው፣
ልጆቻቸውን ቀቀሉ።
כ ካፍ
11 እግዚአብሔር ለመቅሠፍቱ መውጫ በር ከፈተ፤
ጽኑ ቍጣውን አፈሰሰ፤
መሠረቷን እንዲበላ፣
በጽዮን እሳት ለኰሰ።
ל ላሜድ
12ጠላቶችም ሆኑ ወራሪዎች፣
የኢየሩሳሌምን በሮች ጥሰው ይገባሉ ብለው፣
የምድር ነገሥታት፣
ወይም ከዓለም ሕዝብ አንዳቸውም አላመኑም።
מ ሜም
13ይህ ግን ከነቢያት ኀጢአት፣
ከካህናቷም መተላለፍ የተነሣ ሆኗል፤
በውስጧ፣
የጻድቃንን ደም አፍስሰዋልና።
נ ኑን
14እንደ ታወሩ ሰዎች፣
በየመንገዱ ላይ ይደናበራሉ፤
ማንም ሰው ደፍሮ ልብሳቸውን መንካት እስከማይችል ድረስ፣
በደም እጅግ ረክሰዋል።
ס ሳሜክ
15ሰዎች “ሂዱ! እናንት ርኩሳን!” ብለው ይጮኹባቸዋል፤
“ወግዱ! ወግዱ! አትንኩ!” ይሏቸዋል፤
ሸሽተው በሚቅበዘበዙበትም ጊዜ፣
በአሕዛብ መካከል ያሉ ሰዎች፣
“ከእንግዲህ በዚህ መቀመጥ አይገባቸውም!” ይላሉ።
ע ዐዪን
16 እግዚአብሔር ራሱ በትኗቸዋል፤
ከእንግዲህ ወዲያ አይጠብቃቸውም፤
ካህናቱ አልተከበሩም፤
ሽማግሌዎቹም ከበሬታ አላገኙም።
פ ፌ
17ከሁሉም በላይ በከንቱ ርዳታን ስንጠባበቅ፣
ዐይኖቻችን ደከሙ፤
ከግንብ ማማችን ላይ ሆነን፣
ሊያድን ከማይችል ሕዝብ ርዳታ ጠበቅን።
צ ጻዲ
18ሰዎች እግር እግራችንን ተከታተሉን፤
ስለዚህ በመንገዳችን መሄድ አልቻልንም፤
መጨረሻችን ቀርቧል፤ ቀኖቻችንም ተቈጥረዋል፤
ፍጻሜያችን መጥቷልና።
ק ቆፍ
19ከሰማይ ንስሮች ይልቅ፣
ጠላቶቻችን ፈጣኖች ናቸው፤
በተራሮች ላይ አሳደዱን፤
በምድረ በዳም ሸመቁብን።
ר ሬሽ
20 በእግዚአብሔር የተቀባው፣ የሕይወታችን እስትንፋስ፣
በወጥመዳቸው ተያዘ፤
በጥላው ሥር፣
በአሕዛብ መካከል እንኖራለን ብለን አስበን ነበር።
ש ሲን እና ሺን
21አንቺ በዖፅ ምድር የምትኖሪ፣
የኤዶምያስ ሴት ልጅ ሆይ፤ ደስ ይበልሽ፤ ሐሤትም አድርጊ፤
ነገር ግን ለአንቺም ደግሞ ጽዋው ይደርስሻል፤
ትሰክሪያለሽ፤ ዕርቃንሽንም ትጋለጫለሽ።
ת ታው
22የጽዮን ልጅ ሆይ፤ ቅጣትሽ ያበቃል፤
እርሱም የስደትሽን ዘመን አያራዝምም፤
ነገር ግን አንቺ የኤዶምያስ ልጅ ሆይ፤
ኀጢአትሽን ይቀጣል፤
ክፋትሽንም ይፋ ያወጣል።

Currently Selected:

ሰቈቃወ 4: NASV

Highlight

Share

Copy

None

Want to have your highlights saved across all your devices? Sign up or sign in

YouVersion uses cookies to personalize your experience. By using our website, you accept our use of cookies as described in our Privacy Policy