የማርቆስ ወንጌል 15:6-15

የማርቆስ ወንጌል 15:6-15 አማ54

በዚያም በዓል የለመኑትን አንድ እስረኛ ይፈታላቸው ነበር። በዓመፅም ነፍስ ከገደሉት ከዓመፀኞች ጋር የታሰረ በርባን የተባለ ነበረ። ሕዝቡም ወጥተው እንደ ልማዱ ያደርግላቸው ዘንድ እየጮኹ ይለምኑት ጀመር። ጲላጦስም፦ የአይሁድን ንጉሥ እፈታላችሁ ዘንድ ትወዳላችሁን? ብሎ መለሰላቸው፤ የካህናት አለቆች በቅንዓት አሳልፈው እንደ ሰጡት ያውቅ ነበርና። የካህናት አለቆች ግን በርባንን በእርሱ ፈንታ ይፈታላቸው ዘንድ ሕዝቡን አወኩአቸው። ጲላጦስም ዳግመኛ መልሶ፦ እንግዲህ የአይሁድ ንጉሥ የምትሉትን ምን ላደርገው ትወዳላችሁ? አላቸው። እነርሱም ዳግመኛ፦ ስቀለው እያሉ ጮኹ። ጲላጦስም፦ ምን ነው? ያደረገው ክፋት ምንድር ነው? አላቸው። እነርሱ ግን፦ ስቀለው እያሉ ጩኸት አበዙ። ጲላጦስም የሕዝቡን ፈቃድ ሊያደርግ ወዶ በርባንን ፈታላቸው፥ ኢየሱስንም ገርፎ እንዲሰቀል አሳልፎ ሰጠ።

ተዛማጅ ቪዲዮዎች