መጽሐፈ ምሳሌ 6:23-29

መጽሐፈ ምሳሌ 6:23-29 አማ05

የእግዚአብሔር ትእዛዝ፥ እንደ መብራት፥ ትምህርቱም እንደ ብርሃን ያበሩልሃል፤ ተግሣጹ እንዴት መኖር እንደሚቻል ያስተምራል። ከመጥፎ ሴት እንድትርቅና ከሌላ ሰው ሚስት አሳሳች ቃል እንድትጠበቅ ይረዱሃል። ቊንጅናዋን አትመኝ፤ በዐይንዋ ጥቅሻ አትማረክ። አንድ ወንድ ሴትኛ ዐዳሪዋን በአንድ እንጀራ ዋጋ ሊያገኛት ይችላል፤ ከሌላ ሰው ሚስት ጋር ማመንዘር ግን የሕይወት ዋጋ ያስከፍላል። በጉያው እሳት ይዞ ልብሱ የማይቃጠልበት ሰው አለን? እግሩስ ሳይቃጠል ፍም ረግጦ ለመሄድ የሚችል ሰው አለን? ከሌላ ሰው ሚስት ጋር ግንኙነት የሚያደርግ እንደዚሁ ነው፤ የሌላውን ሰው ሚስት የሚነካ ሁሉ ሳይቀጣ አይቀርም።