ከዚህ ሁሉ ነገር በኋላ እግዚአብሔር አብርሃምን ፈተነው፤ እግዚአብሔርም “አብርሃም!” ብሎ ጠራው፤ አብርሃምም “እነሆ፥ አለሁኝ!” ብሎ መለሰ። እግዚአብሔርም “የምትወደውን አንድ ልጅህን ይስሐቅን ይዘህ ወደ ሞሪያ ምድር ሂድ፤ እዚያ በማሳይህ አንድ ኮረብታ ላይ እርሱን መሥዋዕት አድርገህ አቅርብልኝ” አለው። አብርሃም ጠዋት በማለዳ ተነሥቶ ለመሥዋዕቱ የሚሆን እንጨት ቈረጠና በአህያው ላይ ጫነው፤ ከእርሱ ጋር ልጁን ይስሐቅንና ሁለት አገልጋዮችን ይዞ እግዚአብሔር ወዳመለከተው ቦታ ለመሄድ ጒዞ ጀመረ። በሦስተኛው ቀን አብርሃም ቀና ብሎ ሲመለከት ቦታውን በሩቅ አየ። ከዚህ በኋላ አብርሃም አገልጋዮቹን “እናንተ ከአህያው ጋር እዚህ ቈዩ፤ እኔና ልጄ ወደዚያ ሄደን ለእግዚአብሔር ከሰገድን በኋላ እንመለሳለን” አላቸው። አብርሃምም የመሥዋዕቱን እንጨት አንሥቶ ለልጁ ለይስሐቅ አሸከመው፤ እርሱ ግን ቢለዋውንና እሳቱን ያዘ፤ ሁለቱም አብረው ሲሄዱ ሳለ፥ ይስሐቅ አብርሃምን “አባባ!” አለው፤ አብርሃምም “እነሆ፥ አለሁ ልጄ!” አለው። ይስሐቅም “እነሆ፥ እሳትና እንጨት ይዘናል፤ ታዲያ ለመሥዋዕት የሚሆነው በግ የት አለ?” በማለት አብርሃምን ጠየቀው። አብርሃምም “ልጄ ሆይ፥ ለመሥዋዕት የሚሆነውን በግ እግዚአብሔር ለራሱ ያዘጋጃል” አለው፤ ሁለቱም አብረው መንገዳቸውን ቀጠሉ። እግዚአብሔር ወዳመለከተው ቦታ በደረሱ ጊዜ አብርሃም መሠዊያ ሠርቶ እንጨቱን በላዩ ላይ ረበረበው፤ ልጁን ይስሐቅንም አስሮ ከእንጨቱ በላይ በመሠዊያው ላይ አጋደመው። ልጁን ለማረድ ቢላዋ አንሥቶ እጁን ዘረጋ፤ ነገር ግን የእግዚአብሔር መልአክ ከሰማይ “አብርሃም! አብርሃም!” ብሎ ጠራው። አብርሃምም “እነሆ፥ አለሁኝ!” አለ። መልአኩም “ልጁን አትንካ፤ ምንም ዐይነት ጒዳት አታድርስበት፤ አንድ ልጅህን እንኳ ለእኔ ከመስጠት ስለ አልተቈጠብክ እነሆ፥ እኔን እግዚአብሔርን የምትፈራ መሆንህን ተረድቼአለሁ።” አብርሃም ዙሪያውን በተመለከተ ጊዜ ቀንዶቹ በቊጥቋጦ ዛፍ የተያዙ አንድ በግ አየ፤ ሄዶ በጉን አመጣና በልጁ ፋንታ መሥዋዕት አድርጎ አቀረበው። አብርሃም ያንን ቦታ “እግዚአብሔር ያዘጋጃል” ብሎ ሰየመው፤ ዛሬም ቢሆን ሰዎች “እግዚአብሔር በተራራው ላይ ያዘጋጃል” ይላሉ። የእግዚአብሔር መልአክ ሁለተኛ ጊዜ አብርሃምን ጠራውና እንዲህ አለው፤ “እግዚአብሔር ‘ብዙ በረከት እንደምሰጥህ በራሴ ስም እምላለሁ’ ይላል፤ ይህን ስላደረግህና አንድ ልጅህንም ለእኔ ለመስጠት ስላልተቈጠብክ፥ እኔም ዘርህን እንደ ሰማይ ከዋክብትና እንደ ባሕር ዳር አሸዋ አበዛዋለሁ፤ ዘሮችህም ጠላቶቻቸውን ድል ነሥተው ከተሞቻቸውን ይይዛሉ። ትእዛዜን ስለ ፈጸምክ የዓለም ሕዝቦች ሁሉ በዘርህ ይባረካሉ።” ከዚህ በኋላ አብርሃም ወደ አገልጋዮቹ ተመለሰና በአንድነት ሆነው ወደ ቤርሳቤህ ሄዱ፤ አብርሃምም በቤርሳቤህ ተቀመጠ። ከዚህ ሁሉ በኋላ ሚልካ ለወንድሙ ለናኮር ልጆች እንደ ወለደችለት አብርሃም ሰማ፤ እነርሱም፥ የመጀመሪያው ዑፅ፥ ወንድሙም ቡዝ፥ የአራም አባት ቀሙኤል፤ ኬሠድ፥ ሐዞ፥ ፊልዳሽ፥ ይድላፍና በቱኤል ናቸው። በቱኤል ርብቃን ወለደ፤ ሚልካ እነዚህን ስምንት ልጆች ለአብርሃም ወንድም ለናኮር ወለደችለት። ረኡማ የተባለችው የናኮር ቊባት ደግሞ ጤባሕን፥ ገሐምን፥ ተሐሽንና፥ ማዕካን ወለደችለት።
ኦሪት ዘፍጥረት 22 ያንብቡ
ያጋሩ
ሁሉንም ሥሪቶች ያነጻጽሩ: ኦሪት ዘፍጥረት 22:1-24
ጥቅሶችን ያስቀምጡ፣ ያለበይነመረብ ያንብቡ፣ አጫጭር የትምህርት ቪዲዮዎችን ይመልከቱ እና ሌሎችም!
ቤት
መጽሐፍ ቅዱስ
እቅዶች
ቪዲዮዎች