YouVersion Logo
Search Icon

የዮሐንስ ወንጌል መግቢያ

መግቢያ
የዮሐንስ ወንጌል ሥጋ የለበሰው ሕያው የእግዚአብሔር ቃል በሰዎች መካከል እንደተገለጸ ይተነትናል። መጽሐፉ ራሱ እንደሚገልጠው ይህ ወንጌል የተጻፈው አንባቢዎች ኢየሱስ አዳኝ ሆኖ ይመጣል የተባለው የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን እንዲያምኑ ነው፤ በእርሱም በማመናቸው የዘለዓለም ሕይወት እንደሚኖራቸው ሰዎች እንዲረዱ ተጻፈ (20፥31።)
የወንጌሉ መቅድም ዘላለማዊው የእግዚአብሔር ቃልና ኢየሱስ አንድ መሆናቸውን ያሳያል፤ ከዚያም የእግዚአብሔር ልጅ፥ ኢየሱስ የሚሠራቸውን ተአምራት ይዘረዝራል። በተጨማሪም ከእነዚህ ተአምራት ምን ውጤት እንደተገኘ የሚያስረዱት ታሪኮች ይከተላሉ።
በዮሐንስ ወንጌል ውስጥ አንዳንድ ሰዎች በኢየሱስ አምነው የእርሱ ተከታዮች ቢሆኑም፥ ሌሎች ደግሞ መቃወማቸውንና በእርሱ አናምንም ማለታቸውን ማስተዋል ይቻላል። ከምዕራፍ 13-17 ያለው የወንጌል ክፍል የኢየሱስን የስንብት ንግግር አካቷል፤ ይህም ኢየሱስ በተያዘበት ምሽት ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ምን ያኽል የጠበቀ ግንኙነት እንደ ነበረውና በስቅለቱም ዋዜማ የመዘጋጀትና የመጽናናት ቃል እንዳሰማቸው ያሳያል። የመጨረሻዎቹ ምዕራፎች ስለ ኢየሱስ መያዝና ለፍርድ መቅረብ፥ ስለ ስቅለቱና ትንሣኤው፥ እንዲሁም ከትንሣኤው በኋላ ለደቀ መዛሙርቱ ስለ መገለጡ የሚያወሱ ናቸው። በዮሐንስ ወንጌል ውስጥ የኢየሱስ የሕማማቱ ወቅት የክብሩም ሰዓት እንደሆነ በተደጋጋሚ ተገልጿል።
የዮሐንስ ወንጌል በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት የሚገኘውን ዘላለማዊ ሕይወት ጐላ አድርጎ ያሳያል፤ ይህም ጸጋ ከወዲሁ በዚህ ምድር ላይ እንደሚጀምር በማሳየት ነው። ለምሳሌ፥ ኢየሱስ “እኔ የሕይወት እንጀራ ነኝ፤ እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ፤ እኔ መልካም እረኛ ነኝ፤ እኔ መንገድ፥ እውነት፥ ሕይወትም ነኝ” ሲል ጸጋው በዚህ ምድር ላይ መጀመሩን ያሳያል። የዮሐንስን ወንጌል ልዩ ከሚያደርጉት ነገሮች አንዱ መንፈሳዊ እውነቶችን ለማስረዳት የተለመዱና በዕለታዊ ኑሮ የምንጠቀምባቸውን፥ ማለትም እንደ ውሃ፥ እንጀራ፥ ብርሃን፥ እረኛ፥ በጎች፥ የወይን ተክልና የወይን ፍሬ የመሳሰሉ ነገሮችን በምሳሌ መጠቀሙ ነው።
አጠቃላይ የመጽሐፉ ይዘት
መቅድም (1፥1-18)
የልዩ ልዩ ተአምራቶች ወይም ምልክቶች መጽሐፍ (1፥19—12፥50)
የክብር መጽሐፍ (13፥1—20፥31)
የጌታ በገሊላ እንደገና ለደቀ መዛሙርቱ መገለጡ (21፥1-25)
ምዕራፍ

Highlight

Share

Copy

None

Want to have your highlights saved across all your devices? Sign up or sign in