YouVersion Logo
Search Icon

የማርቆስ ወንጌል 16

16
የኢየሱስ ከሞት መነሣት
(ማቴ. 28፥1-8ሉቃ. 24፥1-12ዮሐ. 20፥1-10)
1የሰንበት ቀን ካለፈ በኋላ መግደላዊት ማርያም፥ የያዕቆብ እናት ማርያም ሰሎሜም ሆነው፥ የኢየሱስን አስከሬን ለመቀባት ከመልካም ቅመም የተዘጋጀ ሽቶ ገዙ። 2ከሳምንቱ በመጀመሪያው ቀን እሑድ ጧት በማለዳ፥ ልክ ፀሐይ ስትወጣ፥ ወደ መቃብሩ ሄዱ። 3እነርሱ “ድንጋዩን ከመቃብሩ ደጃፍ ማን አንከባሎ ይከፍትልናል?” በማለት እየተነጋገሩ ይሄዱ ነበር። 4ይህንንም ያሉት መቃብሩ የተዘጋበት ድንጋይ እጅግ ትልቅ ስለ ነበረ ነው፤ ቀና ብለውም በተመለከቱ ጊዜ ግን ድንጋዩ ወደ ጐን ተንከባሎ አዩት። 5ወደ መቃብሩም በገቡ ጊዜ ነጭ ልብስ የለበሰ ጐልማሳ በስተቀኝ በኩል ተቀምጦ በማየታቸው ደነገጡ።
6እርሱ ግን እንዲህ አላቸው፦ “አይዞአችሁ፥ አትደንግጡ፤ እናንተ የምትፈልጉት ተሰቅሎ የነበረውን የናዝሬቱን ኢየሱስን እንደ ሆነ ዐውቃለሁ፤ እርሱ ተነሥቶአል፤ እዚህ የለም፤ የተቀበረበትም ቦታ ይኸውላችሁ፤ ተመልከቱ። 7አሁንም ሂዱ፤ ለደቀ መዛሙርቱና ለጴጥሮስ ‘ከዚህ በፊት ኢየሱስ እንደ ነገራችሁ እርሱ ወደ ገሊላ ቀድሞአችሁ ይሄዳል፤ በዚያም ታዩታላችሁ፤’ ብላችሁ ንገሩአቸው።” #ማቴ. 26፥32፤ ማር. 14፥28።
8ሴቶቹም በፍርሃት እየተንቀጠቀጡ ከመቃብሩ ቦታ ወጥተው ሸሹ፤ እጅግ ፈርተው ስለ ነበር ምንም ነገር ለማንም አልተናገሩም። #16፥8 በአንዳንድ የጥንት መጻሕፍት በዚህ ምዕራፍ በቊ. 8 ቀጥሎ ያለው ቃል ይገኛል፦ ሴቶች ወደ ጴጥሮስና ወደ ጓደኞቹ ሄደው መልአኩ የነገራቸውን ሁሉ አወሩላቸው፤ ከዚህ በኋላ ኢየሱስ ራሱ ለዘለዓለም መዳን የሆነውን፥ የማይለወጠውን ቅዱስ ወንጌል ከፀሐይ መውጫ እስከ መጥለቂያዋ ድረስ በደቀ መዛሙርቱ አማካይነት ላከ።
ኢየሱስ ለመግደላዊት ማርያም መገለጡ
(ማቴ. 28፥9-10ዮሐ. 20፥11-18) #16፥8 አንዳንድ ቅጂዎችና የጥንት ትርጒሞች ከቊ. 9-20 ያለውን ክፍል አይጨምሩም።
[ 9ኢየሱስ ከሳምንቱ በመጀመሪያው ቀን (እሑድ) በማለዳ ከሞት ከተነሣ በኋላ፥ መጀመሪያ ሰባት አጋንንት ላወጣላት ለመግደላዊት ማርያም ታየ። 10እርስዋም ሄዳ፥ በሐዘንና በለቅሶ ላይ ለነበሩት ተከታዮቹ ነገረች። 11እርስዋ “ኢየሱስ ከሞት ተነሥቶ፥ በሕይወት አለ፤ እኔም በዐይኔ አይቸዋለሁ፤” ብላ ነገረቻቸው፤ እነርሱ ግን አላመኑአትም።
ኢየሱስ ለሁለት ደቀ መዛሙርት መታየቱ
(ሉቃ. 24፥13-35)
12ከዚያም በኋላ ወደ ገጠር ይሄዱ ለነበሩ ሁለት ደቀ መዛሙርት ኢየሱስ በሌላ መልክ ታያቸው። 13እነርሱም ተመልሰው ለቀሩት ደቀ መዛሙርት ነገሩአቸው፤ ደቀ መዛሙርቱ ግን እነዚህንም አላመኑአቸውም።
ኢየሱስ ለዐሥራ አንዱ ሐዋርያት መገለጡ
(ማቴ. 28፥16-20ሉቃ. 24፥36-49ዮሐ. 20፥19-23ሐ.ሥ. 1፥6-8)
14ከዚያም በኋላ ዐሥራ አንዱ በማእድ ቀርበው ሲበሉ ኢየሱስ ተገለጠላቸው፤ “ኢየሱስ ከሞት ተነሥቶ በሕይወት አለ፤ በዐይናችንም አይተነዋል፤” ብለው የነገሩአቸውን ባለማመናቸውና በግትርነታቸው ነቀፋቸው። 15እንዲህም አላቸው፦ “ወደ መላው ዓለም ሂዱ፤ ለሰው ሁሉ ወንጌልን አስተምሩ። #ሐ.ሥ. 1፥8። 16ያመነና የተጠመቀ ይድናል፤ የማያምን ግን ይፈረድበታል። 17በእኔ የሚያምኑ ሁሉ እነዚህን ተአምራት ያደርጋሉ፤ በስሜ አጋንንትን ያወጣሉ፤ በአዲስ ቋንቋም ይናገራሉ፤ 18እባቦችን ቢይዙ፥ ወይም የሚገድል መርዝ እንኳ ቢጠጡ አይጐዳቸውም፤ እጃቸውን በበሽተኞች ላይ ሲጭኑ በሽተኞቹ ይድናሉ።”
ኢየሱስ ወደ ሰማይ ማረጉ
(ሉቃ. 24፥50-53ሐ.ሥ. 1፥9-11)
19ጌታ ኢየሱስ ይህን ሁሉ ከነገራቸው በኋላ ወደ ሰማይ ዐረገ። በእግዚአብሔርም ቀኝ ተቀመጠ። #ሐ.ሥ. 1፥9-11። 20ደቀ መዛሙርቱም በየስፍራው ሁሉ እየሄዱ አስተማሩ፤ ጌታም ከእነርሱ ጋር ይሠራ ነበር። ተአምራትንም የማድረግ ሥልጣን በመስጠት የትምህርታቸውን እውነተኛነት ያጸና ነበር።]

Highlight

Share

Copy

None

Want to have your highlights saved across all your devices? Sign up or sign in