YouVersion Logo
Search Icon

የማቴዎስ ወንጌል 23

23
ስለ ሙሴ ሕግ መምህራንና ስለ ፈሪሳውያን ክፋት
(ማር. 12፥38-39ሉቃ. 11፥43-4620፥45-46)
1ከዚህ በኋላ ኢየሱስ ለሕዝቡና ለደቀ መዛሙርቱ እንዲህ ሲል ተናገረ፦ 2“የሕግ መምህራንና ፈሪሳውያን ለማስተማር በሙሴ ወንበር ተቀምጠዋል። 3ስለዚህ እነርሱ የሚሉአችሁን ሁሉ አድርጉ፤ ጠብቁም፤ እነርሱ የሚያደርጉትን ግን አታድርጉ፤ እነርሱ የሚናገሩትን በሥራ ላይ አያውሉትም፤ 4ከባድና አስቸጋሪ ሸክም አስረው በሰው ትከሻ ላይ ይጭናሉ፤ ራሳቸው ግን በጣታቸው እንኳ ሊነኩት አይፈልጉም። 5ሥራቸውን ሁሉ የሚያደርጉት ሰው እንዲያይላቸው ብለው ነው፤ አሸንክታባቸውን ያሰፋሉ፤ የጸሎት ልብሳቸውን ዘርፍ ያስረዝማሉ፤ #ማቴ. 6፥1፤ ዘኍ. 15፥38፤ ዘዳ. 6፥8። 6በግብዣ ላይ የክብር ቦታን፥ በምኲራብም የመጀመሪያ መቀመጫን መያዝ ይወዳሉ። 7በየአደባባዩም ሰው ሁሉ እጅ እንዲነሣቸውና ‘መምህር ሆይ!’ ብሎ እንዲጠራቸው ይፈልጋሉ፤ 8እናንተ ግን መምህራችሁ አንድ ብቻ ስለ ሆነና ሁላችሁም ወንድማማቾች ስለ ሆናችሁ፥ ‘መምህር’ ተብላችሁ አትጠሩ። 9ደግሞም እናንተ ያላችሁ በሰማይ አንድ አባት ብቻ ስለ ሆነ በምድር ላይ ማንንም ‘አባት’ ብላችሁ አትጥሩ። 10ሊቃችሁ ክርስቶስ ብቻ ስለ ሆነ ‘ሊቃውንት’ ተብላችሁ አትጠሩ። 11ከእናንተ መካከል ታላቅ የሆነው የእናንተ አገልጋይ ይሁን። #ማቴ. 20፥26-27፤ ማር. 9፥35፤ 10፥43-44፤ ሉቃ. 22፥26። 12ራሱን ከፍ የሚያደርግ ይዋረዳል፤ ራሱንም ዝቅ የሚያደርግ ከፍ ይላል።” #ሉቃ. 14፥11፤ 18፥14።
የሕግ መምህራንና ፈሪሳውያን እንደ ተወገዙ
(ማር. 12፥40ሉቃ. 11፥39-42445220፥47)
13“ሰው ወደ መንግሥተ ሰማይ እንዳይገባ፥ በሩን የምትዘጉ እናንተ ግብዞች፥ የሕግ መምህራንና ፈሪሳውያን! ወዮላችሁ! እናንተ ራሳችሁ አትገቡበትም፤ መግባት የሚፈልጉትንም እንዳይገቡ ትከለክላላችሁ!”
[ 14“ለታይታ በምታቀርቡት ረዥም ጸሎት እያመካኛችሁ ባሎቻቸው የሞቱባቸውን ሴቶች መተዳደሪያ የምትጨርሱ እናንተ ግብዞች የሕግ መምህራንና ፈሪሳውያን ወዮላችሁ! ስለዚህ እናንተ የባሰ ፍርድ ይደርስባችኋል።] #23፥14 አንዳንድ የብራና ጽሑፎች ቁ. 14 ይጨምራሉ፤ ቃሉም በማር. 12፥40 ያለውን ይመስላል።
15“እናንተ ግብዞች፥ የሕግ መምህራንና ፈሪሳውያን! ወዮላችሁ! አንድን ሰው የእምነታችሁ ተከታይ ለማድረግ በባሕርና በየብስ ትዞራላችሁ፤ ባስገባችሁትም ጊዜ፥ ከእናንተ በሁለት እጥፍ ይብስ ለገሃነም የተዘጋጀ ታደርጉታላችሁ!
16“እናንተ ዕውሮች መሪዎች! ወዮላችሁ! ‘ሰው በቤተ መቅደስ ቢምል፥ ምንም አይደለም’ ትላላችሁ፤ ‘በቤተ መቅደሱ ወርቅ ቢምል ግን በመሐላው ይያዛል’ ትላላችሁ፤ 17እናንተ ሞኞችና ዕውሮች! ከወርቁና ወርቁን ከሚቀድሰው ቤተ መቅደስ የቱ ይበልጣል? 18እንዲሁም ‘ሰው በመሠዊያው ቢምል ምንም አይደለም’፤ ‘በመሠዊያው ላይ ባለው መባ ቢምል ግን በመሐላው ይያዛል’ ትላላችሁ። 19እናንተ ዕውሮች! ከመባውና መባውን ከሚቀድሰው መሠዊያ የቱ ይበልጣል? 20ስለዚህ በመሠዊያው የሚምል፥ በመሠዊያውና በመሠዊያው ላይ ባለው ነገር ሁሉ ይምላል። #23፥20 መባ፦ ሰው ለአምላኩ የሚያቀርበው አገልግሎት ሁሉ መባ ይባላል። 21በቤተ መቅደስም የሚምል፥ በቤተ መቅደሱና በቤተ መቅደሱ ውስጥ በሚኖረው ይምላል። 22በሰማይ የሚምልም በእግዚአብሔር ዙፋንና በዙፋኑ ላይ በሚቀመጠው ይምላል። #ኢሳ. 66፥1፤ ማቴ. 5፥34።
23“እናንተ ግብዞች የሕግ መምህራንና ፈሪሳውያን! ወዮላችሁ! ከአዝሙድ፥ ከእንስላል፥ ከከሙን ዐሥራት ትሰጣላችሁ፤ ነገር ግን በሕግ ውስጥ የሚገኙትን ዋና ዋና ነገሮች ትተዋላችሁ፤ እነርሱም ትክክለኛ ፍርድ፥ ምሕረትና ታማኝነት ናቸው፤ ያንን ሳትተዉ ይህንንም ማድረግ ይገባችሁ ነበር። #ዘሌ. 27፥30። 24እናንተ ዕውሮች መሪዎች! ከምትጠጡትም ሁሉ እንደ ትንኝ ትንሽ የሆነችውን ነገር አጥልላችሁ ትጥላላችሁ፤ እንደ ግመል ትልቅ የሆነውን ነገር ግን ትውጣላችሁ!
25“እናንተ ግብዞች የሕግ መምህራንና ፈሪሳውያን! ወዮላችሁ! ብርጭቆውንና ሳሕኑን ከውጪ በኩል ታጠራላችሁ፤ ውስጡ ግን ቅሚያና ሥሥት የሞላበት ነው፤ 26አንተ ዕውር ፈሪሳዊ! አስቀድመህ ብርጭቆውንና ሳሕኑን ከውስጥ በኩል አጥራ! በዚያን ጊዜ በውጪም በኩል ንጹሕ ይሆናል።
27“እናንተ ግብዞች የሕግ መምህራንና ፈሪሳውያን! ወዮላችሁ! በውስጣቸው በሞቱ ሰዎች አጥንትና በርኩስ ነገር ሁሉ የተሞሉ፥ በውጪ ግን በኖራ ተለስነው የሚያምሩ መቃብሮችን ትመስላላችሁ። #ሐ.ሥ. 23፥3። 28እንዲሁም እናንተ፥ በውጪ ለሰው ጻድቃን መስላችሁ ትታያላችሁ፤ በውስጣችሁ ግን ግብዝነትና ክፋት ሞልቶባችኋል።
29“እናንተ ግብዞች፥ የሕግ መምህራንና ፈሪሳውያን! ወዮላችሁ! የነቢያትን መቃብር ትገነባላችሁ፤ የጻድቃንንም ሐውልት ታስጌጣላችሁ። 30‘በቀድሞ አባቶቻችን ዘመን ተገኝተን ብንሆን ኖሮ የነቢያትን ደም በማፍሰስ ከእነርሱ ጋር ባልተባበርንም ነበር’ ትላላችሁ። 31እንግዲህ፥ ነቢያትን ለገደሉ ሰዎች ልጆቻቸው መሆናችሁን ራሳችሁ ትመሰክራላችሁ። 32እንግዲያውስ አባቶቻችሁ የጀመሩትን እናንተም ፈጽሙ። 33እናንተ እባቦች፥ እባብ ልጆች፥ እንዴት ከገሃነም ቅጣት ማምለጥ ትችላላችሁ? #ማቴ. 3፥7፤ 12፥34፤ ሉቃ. 3፥7። 34ስለዚህ እነሆ፥ እኔ ነቢያትን፥ ጥበበኞችን፥ መምህራንን ወደ እናንተ እልካለሁ፤ ከእነርሱ አንዳንዶቹን ትገድላላችሁ፤ አንዳዶቹን ትሰቅላላችሁ፤ አንዳንዶቹንም በምኲራባችሁ ትገርፋላችሁ፤ ከከተማ ወደ ከተማም ታሳድዱአቸዋላችሁ 35በዚህም ምክንያት ከጻድቁ ከአቤል ደም ጀምሮ በመቅደሱና በመሠዊያው መካከል እስከ ገደላችሁት እስከ በራክዩ ልጅ እስከ ዘካርያስ ደም በምድር ላይ ስለ ፈሰሰው የጻድቃን ደም ቅጣቱ በእናንተ ላይ ይደርሳል፤ #ዘፍ. 4፥8፤ 2ዜ.መ. 24፥20-21። 36በእውነት እላችኋለሁ፤ ይህ ሁሉ ቅጣት በዚህ ትውልድ ላይ ይደርሳል።”
ኢየሱስ ለኢየሩሳሌም እንዳለቀሰ
(ሉቃ. 13፥34-35)
37ቀጥሎም ኢየሱስ እንዲህ አለ፤ “ኢየሩሳሌም፥ ኢየሩሳሌም ሆይ! አንቺ ነቢያትን የምትገድዪ! ወደ አንቺ የተላኩትንም በድንጋይ የምትወግሪ! ዶሮ ጫጩቶችዋን በክንፎችዋ ሥር እንደምትሰበስብ፥ እኔም የአንቺን ልጆች በአንድነት ልሰበስብ ስንት ጊዜ ፈቀድኩ! እናንተ ግን አልፈለጋችሁም። 38እንግዲህ እነሆ፥ ቤታችሁ ወና ሆኖ ይቀራል። #ኤር. 22፥5። 39ስለዚህ ‘በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው’ እስክትሉ ድረስ ከእንግዲህ ወዲህ አታዩኝም እላችኋለሁ።” #መዝ. 118፥26።

Highlight

Share

Copy

None

Want to have your highlights saved across all your devices? Sign up or sign in