ኢሳይያስ 2:1-5
ኢሳይያስ 2:1-5 የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ) (አማ2000)
ስለ ይሁዳና ስለ ኢየሩሳሌም ወደ አሞፅ ልጅ ወደ ኢሳይያስ የመጣ ቃል። በኋላ ዘመን እንዲህ ይሆናል፤ የእግዚአብሔር ቤት በተራሮች ራስ ላይ ይታያል፤ ከኮረብቶችም በላይ ከፍ ከፍ ይላል፤ አሕዛቡም ሁሉ ወደ እርሱ ይመጣሉ። ሕግ ከጽዮን፥ የእግዚአብሔርም ቃል ከኢየሩሳሌም ይወጣልና ብዙዎች አሕዛብ መጥተው፥ “ኑ፤ ወደ እግዚአብሔር ተራራ፥ ወደ ያዕቆብ አምላክ ቤት እንውጣ፤ እርሱም መንገዱን ያስተምረናል፤ በጎዳናውም እንሄዳለን” ይላሉ። በአሕዛብም መካከል ይፈርዳል፤ ብዙ አሕዛብንም ይዘልፋቸዋል፤ ሰይፋቸውንም ማረሻ፥ ጦራቸውንም ማጭድ ለማድረግ ይቀጠቅጣሉ፤ ሕዝብም በሕዝብ ላይ ሰይፍን አያነሣም፤ ሰልፍንም ከእንግዲህ ወዲህ አይማሩም። አሁንም የያዕቆብ ቤት ሆይ፥ ኑ፤ በእግዚአብሔር ብርሃን እንመላለስ።
ኢሳይያስ 2:1-5 አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)
የአሞጽ ልጅ ኢሳይያስ ስለ ይሁዳና ስለ ኢየሩሳሌም ያየው ይህ ነው፤ በዘመኑም ፍጻሜ፣ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ተራራ ከተራሮች ከፍ ብሎ ይመሠረታል፤ ከኰረብቶችም በላይ ከፍ ከፍ ይላል፤ ሕዝቦችም ሁሉ ወደዚያ ይጐርፋሉ። ብዙ አሕዛብ መጥተው እንዲህ ይላሉ፤ “ኑ፤ ወደ እግዚአብሔር ተራራ፣ ወደ ያዕቆብ አምላክ ቤት እንውጣ፤ በጐዳናውም እንድንሄድ፤ መንገዱን ያስተምረናል።” ሕግ ከጽዮን፣ የእግዚአብሔርም ቃል ከኢየሩሳሌም ይወጣልና። እርሱ በሕዝቦች መካከል ይፈርዳል፤ የብዙ ሰዎችን አለመግባባት ያስወግዳል። እነርሱም ሰይፋቸውን ቀጥቅጠው ማረሻ፣ ጦራቸውንም ማጭድ ያደርጋሉ። ሕዝብ በሕዝብ ላይ ሰይፍ አያነሣም፤ ጦርነትንም ከእንግዲህ አይማሩም። እናንተ የያዕቆብ ቤት ሆይ፤ ኑ፤ በእግዚአብሔር ብርሃን እንመላለስ።
ኢሳይያስ 2:1-5 መጽሐፍ ቅዱስ (የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት) (አማ54)
የአሞጽ ልጅ ኢሳይያስ ስለ ይሁዳና ስለ ኢየሩሳሌም ያየው ቃል። በዘመኑም ፍጻሜ የእግዚአብሔር ቤት ተራራ በተራሮች ራስ ላይ ጸንቶ ይቆማል፥ ከኮረብቶችም በላይ ከፍ ከፍ ይላል፥ አሕዛብም ሁሉ ወደ እርሱ ይሰበሰባሉ። ሕግ ከጽዮን የእግዚአብሔርም ቃል ከኢየሩሳሌም ይወጣልና ብዙዎች አሕዛብ ሄደው፦ ኑ፥ ወደ እግዚአብሔር ተራራ፥ ወደ ያዕቆብ አምላክ ቤት እንውጣ፥ እርሱም መንገዱን ያስተምረናል፥ ወደ ጎዳናውም እንሄዳለን ይላሉ። በአሕዛብም መካከል ይፈርዳል፥ በብዙ አሕዛብም ላይ ይበይናል፥ ሰይፋቸውንም ማረሻ ጦራቸውንም ማጭድ ለማድረግ ይቀጠቅጣሉ፥ ሕዝብም በሕዝብ ላይ ሰይፍ አያነሳም፥ ሰልፍም ከእንግዲህ ወዲህ አይማሩም። እናንተ የያዕቆብ ቤት ሆይ፥ ኑ፥ በእግዚአብሔር ብርሃን እንሂድ።
ኢሳይያስ 2:1-5 አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉም (አማ05)
የአሞጽ ልጅ ኢሳይያስ ስለ ይሁዳ አገርና ስለ ኢየሩሳሌም ከተማ የተናገረው ቃል ይህ ነው፦ የዘመኑ ፍጻሜ ሲደርስ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ የተሠራበት ተራራ ከሌሎች ተራራዎች ሁሉ በልጦ ይታያል፤ ከኰረብቶችም ሁሉ እጅግ ከፍ ይላል፤ የብዙ መንግሥታት ሕዝቦች ወደ እርሱ ይጐርፋሉ። ስለዚህ ብዙ ሕዝቦች እንዲህ ይላሉ፦ “ሕግ ከጽዮን፥ የእግዚአብሔርም ቃል ከኢየሩሳሌም ስለሚገኝ ኑ ወደ እግዚአብሔር ተራራ እንውጣ፤ ወደ ያዕቆብ አምላክ ቤተ መቅደስም እንሂድ፤ እርሱ ፈቃዱን እንድናደርግ ያስተምረናል፤ እኛም በእርሱ መንገድ እንሄዳለን።” እርሱ በብዙ መንግሥታት መካከል በመፍረድ አለመግባባትን ያስወግዳል፤ ስለዚህም ሰይፋቸውን ወደ ማረሻ፥ ጦራቸውንም ወደ ማጭድ ይለውጣሉ፤ መንግሥት በመንግሥት ላይ ጦርነት አያነሣም፤ ከዚያም በኋላ የጦር ትምህርት የሚማር አይኖርም። እናንተ የያዕቆብ ልጆች ሆይ! ኑ! በእግዚአብሔር ብርሃን እንመላለስ!
ኢሳይያስ 2:1-5 መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ) (መቅካእኤ)
የአሞጽ ልጅ ኢሳይያስ ስለ ይሁዳና ስለ ኢየሩሳሌም ያየው ይህ ነው፤ በዘመኑም ፍጻሜ፤ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ተራራ ከተራሮች ከፍ ብሎ ይመሠረታል፤ ኰረብቶችም በላይ ከፍ ከፍ ይላሉ፤ ሕዝቦችም ሁሉ ወደዚያ ይጎርፋሉ። ብዙ ሕዝቦችም መጥተው እንዲህ ይላሉ፤ “ኑ፤ ወደ ጌታ ተራራ፤ ወደ ያዕቆብ አምላክ ቤት እንውጣ፤ እርሱ መንገዱን ያስተምረናል፤ በጎዳናውም እንሄዳለን።” ሕግ ከጽዮን፤ የእግዚአብሔር ቃል ከኢየሩሳሌም ይወጣልና። እርሱ በሕዝቦች መካከል ይፈርዳል፤ የብዙ ሰዎችን አለመግባባት ያስወግዳል። እነርሱም ሰይፋቸውን ቀጥቅጠው ማረሻ ጦራቸውንም ማጭድ ያደርጋሉ። ሕዝብ በሕዝብ ላይ ሰይፍ አያነሣም፤ ጦርነትንም ከእንግዲህ አይማሩም። እናንተ የያዕቆብ ቤት ሆይ፤ ኑ፤ በጌታ ብርሃን እንመላለስ።