ዘፍጥረት 35:16-19 - Compare All Versions
ዘፍጥረት 35:16-19 አማ2000 (የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ))
ያዕቆብም ከቤቴል ተጓዘ፤ በጋዲር ግንብ አጠገብ ድንኳን ተከለ፤ ወደ ኤፍራታም ለመድረስ በቀረበ ጊዜ ራሔልን ምጥ ያዛት፤ በምጡም ተጨነቀች። በምጥ ሳለችም አዋላጂቱ፥ “አትፍሪ ይህኛው ደግሞ ወንድ ልጅ ይሆንልሻልና” አለቻት። ከዚያም በኋላ ነፍስዋ ልትወጣ ደረሰች፤ ሞትዋ በእርሱ ሆኖአልና ስሙን የጭንቀቴ ልጅ ብላ ጠራችው ፤ አባቱ ግን ብንያም አለው። ራሔልም ሞተች፤ ወደ ኤፍራታም በምትወስድ መንገድ ተቀበረች፤ እርስዋም ቤተ ልሔም ናት።
ዘፍጥረት 35:16-19 NASV (አዲሱ መደበኛ ትርጒም)
ከዚያም ከቤቴል ተነሥተው ሄዱ፤ ኤፍራታ ለመድረስ ጥቂት ሲቀራቸው ራሔልን ምጥ ያዛት፤ ምጡም ጠናባት። ምጡ አስጨንቋት ሳለ፣ አዋላጇ፣ “አይዞሽ አትፍሪ፤ ሌላ ወንድ ልጅ ልትገላገይ ነው” አለቻት። እርሷ ግን ሕይወቷ ልታልፍ በማጣጣር ላይ ሳለች፣ ልጇን ቤንኦኒ አለችው፤ አባቱ ግን ብንያም አለው። ራሔልም ሞተች፤ ወደ ኤፍራታ በሚወስደው መንገድ በቤተ ልሔም ተቀበረች።
ዘፍጥረት 35:16-19 አማ54 (መጽሐፍ ቅዱስ (የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት))
ከቤቴልም ተነሡ ወደ ኤፍራታም ሊደርሱ ጥቂት ሲቀራቸው ራሔልን ምጥ ያዛት በምጡም ተጨነቀች። ምጡም ባስጨነቅስት ጊዜ አዋላጂቱ፦ አትፍሪ ይኸኛው ደግሞ ወንድ ልጅ ይሆንሻልና አለቻት። እርስዋም ስትሞት ነፍስዋ በምትወጣበት ጊዜ ስሙን ቤንኦኒ ብላ ጠራችው አባቱ ግን ብንያም አለው። ራሔልልም ሞተች ወደ ኤፍራታ በምትወሰድም መንገድ ተቀበረች እርስዋም ቤተልሔም ናት።
ዘፍጥረት 35:16-19 አማ05 (አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉም)
ያዕቆብና ቤተሰቡ ከቤትኤል ለቀው ሄዱ፤ ወደ ኤፍራታ ሊደርሱ ጥቂት ሲቀራቸው የራሔል መውለጃ ጊዜ ደረሰና በከባድ ምጥ ተያዘች። ምጧ እየበረታ በሄደ ጊዜ አዋላጅዋ “ራሔል ሆይ፥ ሌላ ወንድ ልጅ መውለድሽ ስለ ሆነ አይዞሽ አትፍሪ” አለቻት። እርስዋ ግን ልትሞት ታጣጥር ስለ ነበር ከመሞቷ በፊት ልጅዋን “ቤንኦኒ” አለችው፤ አባቱ ግን “ብንያም” አለው። ከዚህ በኋላ ወዲያውኑ ራሔል ሞተች፤ አሁን ቤተ ልሔም ተብሎ በሚጠራው ወደ ኤፍራታ በሚወስደው መንገድ ዳር ተቀበረች።
ዘፍጥረት 35:16-19 መቅካእኤ (መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ))
ከቤቴልም ተነሡ፥ ወደ ኤፍራታም ሊደርሱ ጥቂት ሲቀራቸው ራሔልን ምጥ ያዛት፥ በምጡም ተጨነቀች። ምጡም ባስጨነቃት ጊዜ አዋላጂቱ፦ “አትፍሪ፥ ይኸኛው ደግሞ ወንድ ልጅ ይሆንሻልና” አለቻት። እርሷም ስትሞት ነፍስዋ በምትወጣበት ጊዜ ስሙን “ቤንኦኒ” ብላ ጠራችው፥ አባቱ ግን ብንያም አለው። ራሔልም ሞተች፥ ወደ ኤፍራታ በምትወስድም መንገድ ተቀበረች፥ እርሷም ቤተልሔም ናት።