ዘፍጥረት 14:1-16
ዘፍጥረት 14:1-16 የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ) (አማ2000)
በሰናዖር ንጉሥ በአሚሮፌል፥ በእላሳር ንጉሥ በአርዮክ፥ በኤላም ንጉሥ በኮሎዶጎሞር፥ በአሕዛብ ንጉሥ በቴሮጋል ዘመን እንዲህ ሆነ፤ ከሰዶም ንጉሥ ከባላ፥ ከገሞራ ንጉሥ ከበርሳ፥ ከአዳማ ንጉሥ ከሰናአር፥ ከሲባዮ ንጉሥ ከሲምቦር፤ ሴጎር ከተባለች ከባላ ንጉሥም ጋር ጦርነት አደረጉ። እነዚህ ሁሉ በኤሌቄን ሸለቆ ተሰብስበው ተባበሩ፤ ይኸውም የጨው ባሕር ነው። ዐሥራ ሁለት ዓመት ለኮሎዶጎሞር ተገዙ፤ በዐሥራ ሦስተኛውም ዓመት ዐመፁ። በዐሥራ አራተኛውም ዓመት ኮሎዶጎሞርና ከእርሱ ጋር የነበሩት ነገሥታት መጡ፤ ረዐይትን በአስጣሮት ቃርናይም፥ ከእነርሱም ጋር ጽኑዓን ሰዎችንና ኦሚዎስን በሴዊ ከተማ ገደሉአቸው፤ በሴይር ተራራዎች ያሉ የኬሬዎስ ሰዎችንም በበረሃ አጠገብ እስከ አለችው እስከ ፋራን ዛፍ ድረስ መቱአቸው። ተመልሰውም ቃዴስ ወደ ተባለች ወደ ፍርድ ምንጭ መጡ፤ የአማሌቅን አለቆች ሁሉና በአሳሶን ታማር የሚኖሩ አሞራውያንንም ገደሉአቸው። የሰዶም ንጉሥና የገሞራ ንጉሥ፥ የአዳማ ንጉሥና የሲባዮን ንጉሥ፥ ሴጎር የተባለች የባላቅ ንጉሥም ወጡ፤ እነዚህ ሁሉ በጨው ሸለቆ በእነርሱ ላይ ለሰልፍ ወጡ፤ ከኤላም ንጉሥ ከኮሎዶጎሞር፥ ከአሕዛብ ንጉሥ ከቴሮጋል፥ ከሰናዖር ንጉሥ ከአሜሮፌል፥ ከእላሳር ንጉሥ ከአርዮክ ጋር ተጋጠሙ። እነዚህ አራቱ ነገሥታት ከአምስቱ ነገሥታት ጋር ተዋጉ። ያም የጨው ሸለቆ የዝፍት ጕድጓዶች ነበሩበት። የሰዶም ንጉሥና የገሞራ ንጉሥም ሸሹና በዚያ ወደቁ፤ የቀሩትም ወደ ተራራማው ሀገር ሸሹ። የሰዶምንና የገሞራን ፈረሶች ሁሉ፥ ስንቃቸውንም ሁሉ ይዘው ሄዱ። እነርሱም የአብራምን የወንድም ልጅ ሎጥንና ገንዘቡን ይዘው ሄዱ። እርሱ በሰዶም ይኖር ነበርና። ከአመለጡትም አንድ ሰው መጣ፤ ለዕብራዊው ለአብራምም ነገረው፤ እርሱም የኤስኮል ወንድምና የአውናን ወንድም በሆነ በአሞራዊው የመምሬ ዛፍ ይኖር ነበር፤ እነዚያም ከአብራም ጋር ቃል ኪዳን ገብተው ነበር። አብራምም የወንድሙ ልጅ ሎጥ እንደ ተማረከ በሰማ ጊዜ ወገኖቹንና ቤተሰቦቹን ሁሉ ቈጠራቸው፤ እነርሱም ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት ሆኑ፤ እስከ ዳን ድረስ ተከትሎ አሳደዳቸው። እርሱም ከብላቴኖቹ ጋር በሌሊት ደረሰባቸው፤ መታቸውም፤ በደማስቆ ግራ እስካለችውም እስከ ሖባ ድረስ አሳደዳቸው። የሰዶምን ፈረሶች ሁሉ አስመለሰ፤ ደግሞም የወንድሙን ልጅ ሎጥንና ንብረቱን፥ ሴቶችንና ሕዝቡንም አስመለሰ።
ዘፍጥረት 14:1-16 አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)
አምራፌል የሰናዖር ንጉሥ፣ አርዮክ የእላሳር ንጉሥ፣ ኮሎዶጎምር የኤላም ንጉሥ፣ ቲድዓል የጎይም ንጉሥ በነበሩበት ዘመን፣ ከሰዶም ንጉሥ ከበላ፣ ከገሞራ ንጉሥ ከብርሳ፣ ከአዳማ ንጉሥ ከሰነአብ፣ ከስቦይ ንጉሥ ከሰሜበር፣ እንዲሁም ዞዓር ከተባለች ከቤላ ንጉሥ ጋራ ለመዋጋት ወጡ። እነዚህ የኋለኞቹ ዐምስቱ ነገሥታት በሲዲም ሸለቆ፣ በጨው ባሕር ተሰበሰቡ። እነርሱም ዐሥራ ሁለት ዓመት ለኮሎዶጎምር ከተገዙ በኋላ በዐሥራ ሦስተኛው ዓመት ዐመፁ። በዐሥራ አራተኛው ዓመት ኮሎዶጎምርና ከርሱ ጋራ የተባበሩት ነገሥታት ወጡ፤ ራፋይምን በአስጣሮት ቃርናይም፣ ዙዚምን በሃም፣ ኤሚማውያን በሴዊ ቂርያታይም፣ የሖሪ ሰዎችንም በተራራማው አገር በሴይር በረሓማ አጠገብ እስካለው እስከ ኤልፋራን ድረስ ድል አደረጓቸው። ከዚያም ተመልሰው ዓይንሚስፖጥ ወደተባለው ወደ ቃዴስ መጡ፤ የአማሌቃውያንና በሐሴሶን ታማር ይኖሩ የነበሩትን የአሞራውያንን ግዛት በሙሉ ድል አድርገው ያዙ። ከዚያም የሰዶም፣ የገሞራ፣ የአዳማ፣ የስቦይ እንዲሁም ዞዓር የተባለችው የቤላ ነገሥታት በሲዲም ሸለቆ ሰራዊታቸውን አስተባበሩ። እነዚህ ዐምስቱ፣ በኤላም ንጉሥ በኮሎዶጎምር፣ በጎይም ንጉሥ በቲድዓል፣ በሰናዖር ንጉሥ በአምራፌል፣ በእላሳር ንጉሥ በአርዮክ፣ በእነዚህ በአራቱ ላይ ዘመቱባቸው። በሲዲም ሸለቆ ብዙ የቅጥራን ጕድጓዶች ስለ ነበሩ የሰዶምና የገሞራ ነገሥታት ሲሸሹ ከሰዎቻቸው አንዳንዶቹ በእነዚህ ጕድጓዶች ውስጥ ወደቁ፤ የቀሩትም ወደ ተራሮች ሸሹ። አራቱ ነገሥታትም በሰዶምና በገሞራ ያገኙትን ሀብትና ምግብ ሁሉ ዘርፈው ሄዱ። የአብራም ወንድም ልጅ ሎጥ፣ ሰዶም ይኖር ስለ ነበር እርሱንም ማርከው ንብረቱንም ዘርፈው ሄዱ። ከዚህም ያመለጠ አንድ ሰው መጥቶ ለዕብራዊው ለአብራም ይህን ነገረ፤ አብራም በዚያ ጊዜ ይኖር የነበረው በአሞራዊው መምሬ ታላላቅ ዛፎች አጠገብ ነበር። መምሬ፣ ወንድሞቹ ኤስኮልና አውናን የአብራም የኪዳን አጋሮቹ ነበሩ። አብራም የወንድሙን ልጅ መማረክ እንደ ሰማ በቤቱ ተወልደው አድገው የሠለጠኑ 318 ጦረኞች አሰልፎ እስከ ዳን ድረስ ገሠገሠ። አብራም ጠላቶቹን ለማጥቃት ሰራዊቱን ሌሊቱን በቡድን በቡድን ከፋፍሎ ከደማስቆ በስተሰሜን እስከሚገኘው እስከ ሖባ ድረስ አሳደዳቸው። አብራም ጠላት የማረከውን በሙሉ አስጣለ፤ የወንድሙን ልጅ ሎጥን፣ ንብረቱን እንዲሁም ሴቶቹንና ሌሎቹን ምርኮኞች አስመለሰ።
ዘፍጥረት 14:1-16 መጽሐፍ ቅዱስ (የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት) (አማ54)
በሰናዖር ንጉሥ በአምራፌል፥ በእላሳር ንጉሥ በአርዮክ፥ በኤላም ንጉሥ በኮሎዶጎምር፥ በአሕዛብ ንጉሥ በቲድዓል ዘመን እንዲህ ሆነ ከሰዶም ንጉሥ ከባላ፥ ከገሞራ ንጉሥ ከብርሳ፥ ከአዳማ ንጉሥ ከሰሜበር፥ ዞዓር ከተባለች ከቤላ ንግሥም ጋር ሰልፍ አደረጉ። እነዚህ ሁሉ በሲዲም ሸለቆ ተሰብስበው ተባበሩ፤ ይኸውም የጨው ባሕር ነው። አሥራ ሁለት ዓመት ለኮሎዶጎምር ተገዝተው ነበር፥ በአሥራ ሦስተኛውም ዓመት ዐመፁ። በአሥራ አራተኛውም ዓመት ኮሎዶጎምርና ከእርሱ ጋር የነበሩት ነገሥታት መጡ፤ ራፋይምን በአስጣሮት ቃርናይ፥ ዙዚምንም በሃም፥ ኤሚምንም በሴዊ ቂርያታይም መቱ፤ የሖር ሰዎችንም በሴይር ተራራቸው በበረሀ አጠገብ እስካለች እስከ ኤል ፋራን ድረስ መቱ። ተመልሰውም ቃዴስ ወደ ተባለች ወደ ዓይንሚስፓጥ መጡ፤ የአማሌቅን አገር ሁሉና ደግሞ በሐሴሶን ታማር የነበረውን አሞራውያንን መቱ። የሰዶም ንጉሥና የገሞራ ንጉሥ፥ የአዳማ ንጉሥና የሰቦይም ንጉሥ፥ ዞዓር የተባለች የቤላ ንጉሥም ወጡ፤ እነዚህ ሁሉ በሲዲም ሸለቆ በእነርሱ ላይ ለሰልፍ ወጡ፤ የኤላምን ንጉሥ ኮሎዶጎምርን፤ የአሕዛብን ንጉሥ ቲድዓልን፤ የሰናዖርን ንጉሥ አምራፌልን፥ የእላሳርን ንጉሥ አርዮክን ለመውጋት አምስቱ ነገሥታት በእነዚህ በአራቱ ላይ ወጡ። በሲዲም ሸለቆ ግን የዝፍር ጕድጓዶች ነበሩበት። የሰዶም ንጉሥ የገሞራ ንጉሥም ሸሹ። የሰዶምንና የገሞራንን ከብት ሁሉ መብላቸውንም ሁሉ ወስደው ሄዱ። በሰዶም ይኖር የነበረውን የአብራምን የወንድም ልጅ ሎጥን ደግሞ ከብቱንም ወስደው ሄዱ። አንድ የሸሸ ስውም መጣ፥ ለዕብራዊው ለአብራምም ነገረው እርሱም የኤስኮል ወንድምና የአውናን ወንድም በሆነ በአሞራዊ መምሬ የአድባር ዛፍ ይኖር ነበር። አብራምም ወንድሙ እንደ ተማረከ በሰማ ጊዜ በቤቱ የተወለዱትን ሦስት መቶ አሥራ ስምንት ብላቴኖቹን አሰለፈ፥ ፍለጋቸውንም ተለትሎ እስከ ዳን ድረስ ሄደ። ብላቴኖቹንም ከፍሎ በሌሊት እርሱ ከባሪያዎቹ ጋር ወረደባቸው፥ መታቸውም፥ በደማስቆ ግራ እስካለችውም እስከ ሖባ ድረስ አሳደዳቸው። ከብቱንም ሁሉ አስመለሰ፥ ደግሞም ወንድሙን ሎጥንና ከብቶቹን ሴቶችንና ሕዝቡን ደግሞ መለሰ።
ዘፍጥረት 14:1-16 አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉም (አማ05)
በዚያን ጊዜ የባቢሎን ንጉሥ አምራፌል፥ የኤላሳር ንጉሥ አርዮክ፥ የዔላም ንጉሥ ከዶርላዖሜር፥ የጎይም ንጉሥ ቲድዓል ነበሩ፤ እነዚህ አራቱ ነገሥታት፥ ሌሎችን አምስት ነገሥታት ለመውጋት ሄዱ፤ የተዘመተባቸውም አምስት ነገሥታት የሰዶም ንጉሥ ቤራዕ፥ የገሞራ ንጉሥ ቢርሻዕ፥ የአዳማ ንጉሥ ሺንአብ፥ የጸቦይም ንጉሥ ሼሜቤርና ጾዓር ተብላ የምትጠራው የቤላዕ ንጉሥ ነበሩ። እነዚህ ነገሥታት አንድ ግንባር ፈጥረው አሁን ሙት ባሕር ተብሎ በሚጠራው በሲዲም ሸለቆ ጦርነት ገጠሙ፤ እነዚህ ነገሥታት ለዐሥራ ሁለት ዓመት በከዶርላዖሜር ቊጥጥር ውስጥ ነበሩ፤ በዐሥራ ሦስተኛው ዓመት ግን በእርሱ ላይ ዐመፁ። በዐሥራ አራተኛው ዓመት ከዶርላዖሜርና ከእርሱ ጋር የተባበሩት ነገሥታት ከነሠራዊቶቻቸው መጥተው ረፋያውያንን በዐስታሮት ቃርናይም፥ ዙዛውያንን በሃም፥ ኤማውያንን በሻዌ ቂርያታይም፥ የሖር ሰዎችንም በተራራማው አገር በኤዶም፥ በበረሓ አጠገብ እስካለው እስከ ኤልፋራን ባለው ስፍራ ድል ነሡአቸው። ከዚያም ተመልሰው ወደ ቃዴስ መጡ፤ በዚያን ጊዜ የዚህ ቦታ ስም ዔይንሚሽፖጥ ይባል ነበር። የዐማሌቃውያንንም ምድር ሁሉ ያዙ፤ በሐጸጾን ታማር ይኖሩ የነበሩትን አሞራውያንንም አሸነፉ። ከዚህ በኋላ የሰዶም፥ የገሞራ፥ የአዳማ፥ የጸቦይምና የቤላዕ ነገሥታት ሠራዊታቸውን በሲዲም ሸለቆ አሰልፈው ተዋጉ፤ የተዋጉትም ከዔላም፥ ከጎይም፥ ከባቢሎንና ከኤላሳር ነገሥታት ጋር ነበር፤ አምስቱ ነገሥታት ከአራቱ ነገሥታት ጋር የተዋጉት በዚህ ዐይነት ነበር። በሲዲም ሸለቆ ብዙ የቅጥራን ጒድጓዶች ነበሩ፤ ስለዚህ የሰዶምና የገሞራ ነገሥታት ከጦርነቱ ሸሽተው ለማምለጥ በሞከሩ ጊዜ በጒድጓዶቹ ውስጥ ወደቁ፤ የቀሩት ሦስት ነገሥታት ግን ወደ ተራራዎቹ ሸሹ። አራቱ ነገሥታት በሰዶምና በገሞራ ያገኙትን ነገር ሁሉ ምግብ እንኳ ሳይቀር ማርከው ሄዱ። የአብራም የወንድም ልጅ ሎጥ በሰዶም ይኖር ስለ ነበር እርሱን ማርከው፥ ሀብቱንም ሁሉ ይዘው ሄዱ። ነገር ግን አንድ ሰው ሸሽቶ መጣና የሆነውን ሁሉ ለዕብራዊው ለአብራም ነገረው፤ በዚያን ጊዜ አብራም የሚኖረው በአሞራዊው መምሬ የተቀደሱ የወርካ ዛፎች አጠገብ ነበር፤ መምሬና ወንድሞቹ ኤሽኮል፥ ዐኔር የአብራም የጦር ቃል ኪዳን ጓደኞች ነበሩ። አብራም የወንድሙ ልጅ እንደ ተማረከ በሰማ ጊዜ በቤቱ ተወልደው የጦር ልምምድ ያላቸውን 318 ሰዎች በትጥቅ አደራጅቶ አራቱን ነገሥታት በመከታተል እስከ ዳን ድረስ ሄደ። እዚያ ሰዎቹን በቡድን ከፋፍሎ እርሱና አገልጋዮቹ ከጠላቶቹ ጋር በሌሊት ጦርነት ገጥመው ድል አደረጋቸው፤ ከደማስቆ በስተሰሜን እስከሚገኘው እስከ ሖባ ድረስ አሳደዳቸው። የተወሰደውንም ምርኮ ሁሉ መልሶ አመጣ፤ እንዲሁም የወንድሙን ልጅ ሎጥን ከነሀብቱ መልሶ አመጣ፤ ከእነርሱም ጋር ሴቶችና ሌሎች እስረኞች ነበሩ።
ዘፍጥረት 14:1-16 መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ) (መቅካእኤ)
በሰናዖር ንጉሥ በአምራፌል፥ በእላሳር ንጉሥ በአርዮክ፥ በኤላም ንጉሥ በኮሎዶጎምር፥ በአሕዛብ ንጉሥ በቲድዓል ዘመን እንዲህ ሆነ ከሰዶም ንጉሥ ከባላ፥ ከገሞራ ንጉሥ ከብርሳ፥ ከአዳማ ንጉሥ ከሰነአብ፥ ከሰቦይም ንጉሥ ከሰሜበር፥ ዞዓር ከተባለች ከቤላ ንጉሥም ጋር ሰልፍ አደረጉ። እነዚህ ሁሉ በሲዲም ሸለቆ ተሰብስበው ተባበሩ፥ ይኸውም የጨው ባሕር ነው። ዐሥራ ሁለት ዓመት ለኮሎዶጎምር ተገዝተው ነበር፥ በዓሥራ ሦስተኛውም ዓመት ዐመፁ። በዓሥራ አራተኛውም ዓመት ኮሎዶጎምርና ከእርሱ ጋር የነበሩት ነገሥታት መጡ፥ ራፋይምን በአስጣሮት ቃርናይም፥ ዙዚምንም በሃም፥ ኤሚምንም በሴዊ ቂርያታይም መቱ፥ የሖር ሰዎችንም በሴይር ተራራቸው በበረሀ አጠገብ እስካለች እስከ ኤል ፋራን ድረስ መቱ። ተመልሰውም ቃዴስ ወደተባለች ወደ ዓይንሚስፓጥ መጡ፥ የአማሌቅን አገር ሁሉና ደግሞ በሐሴቦን ታማር የነበረውን አሞራውያንን መቱ። የሰዶም ንጉሥና የገሞራ ንጉሥ፥ የአዳማ ንጉሥና የሰቦይም ንጉሥ፥ ዞዓር የተባለች የቤላ ንጉሥም ወጡ፥ እነዚህ ሁሉ በሲዲም ሸለቆ በእነርሱ ላይ ለሰልፍ ወጡ፥ የኤላምን ንጉሥ ኮሎዶጎምርን፥ የአሕዛብን ንጉሥ ቲድዓልን፥ የሰናዖርን ንጉሥ አምራፌልን፥ የእላሳርን ንጉሥ አርዮክን ለመውጋት አምስቱ ነገሥታት በእነዚህ በአራቱ ላይ ወጡ። በሲዲም ሸለቆ ግን የዝፍት ጉድጓዶች ነበሩበት። የሰዶም ንጉሥ የገሞራ ንጉሥም ሸሹና ወደዚያ ወደቁ፥ የቀሩትም ወደ ተራራ። ሸሹ። የሰዶምንና የገሞራን ከብት ሁሉ መብላቸውንም ሁሉ ወስደው ሄዱ። በሰዶም ይኖር የነበረውን የአብራምን የወንድም ልጅ ሎጥን ደግሞ ከብቱንም ወስደው ሄዱ። አንድ የሸሸ ሰውም መጣ፥ ለዕብራዊው ለአብራምም ነገረው፥ እርሱም የኤስኮል ወንድምና የአውናን ወንድም በሆነ በአሞራዊ መምሬ የባሉጥ ዛፎች አጠገብ ይኖር ነበር፥ እነዚያም ከአብራም ጋር ቃል ኪዳን ገብተው ነበር። አብራምም ወንድሙ እንደ ተማረከ በሰማ ጊዜ በቤቱ የተወለዱትን ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት ብላቴኖቹን አሰለፈ፥ ፍለጋቸውንም ተከትሎ እስከ ዳን ድረስ ሄደ። አብራምም ጠላቶቹን ለማጥቃት አገልጋዮቹን በቡድን ከፋፍሎ በሌሊት እርሱ ከባርያዎቹ ጋር ወረደባቸው፥ መታቸውም፥ በደማስቆ ግራ እስካለችውም እስከ ሖባ ድረስ አሳደዳቸው። ከብቱንም ሁሉ አስመለሰ፥ ደግሞም ወንድሙን ሎጥንና ከብቶቹን ሴቶችንና ሕዝቡን ደግሞ መለሰ።