አስቴር 4:13-17
አስቴር 4:13-17 አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)
እርሱም ይህን መልስ ላከባት፤ “አንቺ በንጉሥ ቤት በመሆንሽ ብቻ ሌላው የአይሁድ ሕዝብ ሲጠፋ አንቺ የምትተርፊ እንዳይመስልሽ፤ በዚህ ጊዜ አንቺ ዝም ብትዪ፣ ለአይሁድ ርዳታና ትድግና ከሌላ ስፍራ ይመጣላቸዋል፤ አንቺና የአባትሽ ቤት ግን ትጠፋላችሁ፤ ደግሞስ አንቺ ንግሥት ለመሆን የበቃሽው ለዚህ ጊዜ እንደ ሆነ ማን ያውቃል?” ከዚያም አስቴር ለመርዶክዮስ ይህን መልስ ላከችበት፤ “ሂድና በሱሳ ያሉትን አይሁድ ሁሉ በአንድነት ሰብስብ፤ ስለ እኔም ጹሙልኝ፤ ቀንም ይሁን ሌሊት ለሦስት ቀን አትብሉ፤ አትጠጡም። እኔና ደንገጡሮቼም እናንተ እንደምታደርጉት ሁሉ እንጾማለን፤ ይህ ከተፈጸመ በኋላ ግን ነገሩ ምንም እንኳ ከሕግ ውጭ ቢሆንም፣ ወደ ንጉሡ ዘንድ እሄዳለሁ፤ ከጠፋሁም ልጥፋ።” ስለዚህ መርዶክዮስ ሄደ፤ የአስቴርንም ትእዛዝ ሁሉ ፈጸመ።
አስቴር 4:13-17 መጽሐፍ ቅዱስ (የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት) (አማ54)
መርዶክዮስም አክራትዮስን፦ ሂድና ለአስቴር እንዲህ በላት አለው፦ አንቺ፦ በንጉሥ ቤት ስለ ሆንሁ ከአይሁድ ሁሉ ይልቅ እድናለሁ ብለሽ በልብሽ አታስቢ። በዚህ ጊዜ ቸል ብትዪ ዕረፍትና መዳን ለአይሁድ ከሌላ ስፍራ ይሆንላቸዋል፥ አንቺና የአባትሽ ቤት ግን ትጠፋላችሁ፥ ደግሞስ ወደ መንግሥት የመጣሽው እንደዚህ ላለው ጊዜ እንደ ሆነ ማን ያውቃል? አስቴርም እንዲህ ብሎ ለመርዶክዮስ እንዲመልስ አዘዘችው፦ ሄደህ በሱሳ ያሉትን አይሁድ ሁሉ ሰብስብ፥ ለእኔም ጹሙ፥ ሦስት ቀን ሌሊቱንና ቀኑን አትብሉም፥ አትጠጡም፥ እኔና ደንገጥሮቼ ደግሞ እንዲሁ እንጾማለን፥ ምንም እንኳ ያለ ሕግ ቢሆን ወደ ንጉሡ እገባለሁ፥ ብጠፋም እጠፋለሁ። መርዶክዮስም ሄዶ አስቴር እንዳዘዘችው ሁሉ አደረገ።
አስቴር 4:13-17 አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉም (አማ05)
ከዚህ የሚከተለውን ማስጠንቀቂያ ላከባት፤ “አንቺ በቤተ መንግሥት ለመኖር በመቻልሽ ከሌሎች አይሁድ የተሻለ ዋስትና ያለሽ አይምሰልሽ፤ እንደዚህ ባለ ጊዜ ችላ ብለሽ ዝም ብትዪ፥ ለአይሁድ ከሌላ ቦታ ርዳታ መምጣቱ አይቀርም፤ እነርሱም በእርግጥ ይድናሉ፤ አንቺ ግን ትሞቻለሽ፤ የአባትሽም የቤተሰብ ሐረግ ተቋርጦ ይቀራል፤ ነገር ግን አንቺ ንግሥት የሆንሽው በዚህ መከራ ጊዜ እኛን ለመታደግ እንደ ሆነ ማን ያውቃል?” አስቴርም ለመርዶክዮስ እንዲህ ስትል መለሰችለት፦ “ሄደህ በሱሳ የሚገኙትን አይሁድ በአንድነት ሰብስብ፤ ጾም ዐውጃችሁም ለእኔ ጸልዩ፤ እስከ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት ምንም ዐይነት ምግብ አትብሉ፤ ምንም ዐይነት መጠጥ አትጠጡ፤ እኔና ደንገጡሮቼም በዚሁ ዐይነት እንቈያለን፤ ከዚህም በኋላ በሕግ የተከለከለ ቢሆንም ደፍሬ ወደ ንጉሡ ዘንድ እገባለሁ፤ ይህን በማድረጌ ብሞትም ልሙት።” መርዶክዮስም ተነሥቶ ሄደ፤ አስቴር በነገረችውም መሠረት ሁሉን ነገር አደረገ።