አንደኛ መጽሐፈ ነገሥት 19:15-21

አንደኛ መጽሐፈ ነገሥት 19:15-21 አማ54

እግዚአብሔርም አለው “ሂድ፤ በመጣህበትም መንገድ በምድረ በዳ ወደ ደማስቆ ተመለስ፤ ከዚያም በደረስህ ጊዜ በሶርያ ላይ ንጉሥ ይሆን ዘንድ አዛሄልን ቅባው፤ በእስራኤልም ላይ ንጉሥ ይሆን ዘንድ የናሜሲን ልጅ ኢዩን ቅባው፤ በፋንታህም ነቢይ ይሆን ዘንድ የአቤልምሖላን ሰው የሣፋጥን ልጅ ኤልሳዕን ቅባው። ከአዛሄልም ሰይፍ ያመለጠውን ሁሉ፥ ኢዩ ይገድለዋል፤ ከኢዩም ሰይፍ ያመለጠውን ሁሉ ኤልሳዕ ይገድለዋል። እኔም ከእስራኤል ጕልበታቸውን ለበኣል ያላንበረከኩትን ሁሉ፥ በአፋቸውም ያልሳሙትን ሁሉ፥ ሰባት ሺህ ሰዎች ለእኔ አስቀራለሁ።” ከዚያም ሄደ፤ የሣፋጥንም ልጅ ኤልሳዕን በዐሥራ ሁለት ጥማድ በሬዎች ሲያርስ፥ እርሱም ከዐሥራ ሁለተኛው ጋር ሆኖ አገኘው። ኤልያስም ወደ እርሱ አልፎ መጎናጸፊያውን ጣለበት። በሬዎቹንም ተወ፤ ከኤልያስም በኋላ ሮጦ “አባቴንና እናቴን እስማቸው ዘንድ፥ እባክህ ተወኝ፤ ከዚያም በኋላ እከተልሃለሁ፤” አለው። እርሱም “ሂድና ተመለስ፤ ምን አድርጌልሃለሁ?” አለው። ከእርሱም ዘንድ ተመልሶ ሁለቱን በሬዎች ወስዶ አረዳቸው፤ ሥጋቸውንም በበሬዎቹ ዕቃ ቀቀለው፤ ለሕዝቡም ሰጣቸው፤ በሉም፤ እርሱም ተነሥቶ ኤልያስን ተከትሎ ሄደ፤ ያገለግለውም ነበር።