ሰባተኛውም ወር በደረሰ ጊዜ የእስራኤል ልጆች በከተሞቻቸው ነበሩ። ሕዝቡም ሁሉ በውኃው በር ፊት ወዳለው አደባባይ እንደ አንድ ሰው ሆነው ተሰበሰቡ፤ እግዚአብሔርም ለእስራኤል ያዘዘውን የሙሴን ሕግ መጽሐፍ ያመጣ ዘንድ ጸሓፊውን ዕዝራን ነገሩት። ካህኑም ዕዝራ በሰባተኛው ወር በመጀመሪያው ቀን ሕጉን በወንዶችና በሴቶች ጉባኤ፥ አስተውለውም በሚሰሙት ሁሉ ፊት አመጣው። በውኃውም በር ፊት ባለው አደባባይ ላይ ቆሞ፥ በወንዶችና በሴቶች በሚያስተውሉትም ፊት፥ ከማለዳ ጀምሮ እስከ ቀትር ድረስ አነበበው፤ የሕዝቡም ሁሉ ጆሮ የሕጉን መጽሐፍ ለመስማት ያደምጥ ነበር። ጸሓፊውም ዕዝራ ስለዚህ ነገር በተሠራ በዕንጨት መረባርብ ላይ ቆሞ ነበር፤ በአጠገቡ መቲትያ፥ ሰምያ፥ ሐናንያ፤ ኦርያ፥ ሕልቅያ፥ መዕሢያ በቀኙ በኩል፥ ፈድያ፥ ሚሳኤል፥ ሚልክያ፥ ሐሱም፥ ሐስበዳና፥ ዘካርያስ፥ ሜሱላም በግራው በኩል ቆመው ነበር። ዕዝራም የሕዝቡ ሁሉ የበላይ ነበረና በሕዝቡ ሁሉ ፊት መጽሐፉን ገለጠ፤ በገለጠውም ጊዜ ሕዝቡ ሁሉ ቆሙ። ዕዝራም ታላቁን አምላክ እግዚአብሔርን አመሰገነ፤ ሕዝቡም ሁሉ እጃቸውን እየዘረጉ፥ “አሜን፥ አሜን” ብለው መለሱ። ራሳቸውንም አዘነበሉ፤ በግንባራቸውም ወደ ምድር ተደፍተው ለእግዚአብሔር ሰገዱ። ደግሞ ኢያሱና ባኒ፥ ሰራብያ፥ ያሚን፥ ዓቁብ፥ ሳባታይ፥ ሆዲያ፥ መዕሤያ፥ ቆሊጣ፥ ዓዛርያ፥ ኢዮዛባድ፥ ሐናን፥ ፌልዕያ፥ ሌዋውያኑም ሕጉን ለሕዝቡ ያስተምሩ ነበር፤ ሕዝቡም በየስፍራቸው ቆመው ነበር። የእግዚአብሔርንም ሕግ መጽሐፍ አነበቡ፤ ዕዝራም እግዚአብሔርን ማወቅ ያስተምርና ያስታውቅ ነበር፤ ሕዝቡም የሚነበበውን ያስተውሉ ነበር።
መጽሐፈ ነህምያ 8 ያንብቡ
ያጋሩ
ሁሉንም ሥሪቶች ያነጻጽሩ: መጽሐፈ ነህምያ 8:1-8
ጥቅሶችን ያስቀምጡ፣ ያለበይነመረብ ያንብቡ፣ አጫጭር የትምህርት ቪዲዮዎችን ይመልከቱ እና ሌሎችም!
ቤት
መጽሐፍ ቅዱስ
እቅዶች
ቪዲዮዎች