መጽሐፈ ሳሙኤል ካልእ 22
22
የዳዊት መዝሙር ከጠላቶቹ በዳነ ጊዜ
(መዝ. 17)
1ዳዊትም እግዚአብሔር ከሳኦል እጅና ከጠላቶቹ ሁሉ እጅ ባዳነው ቀን የዚህን መዝሙር ቃል ለእግዚአብሔር ተናገረ።
2እንዲህም አለ፥ “እግዚአብሔር ዓለቴ፥ አምባዬም፥ መድኀኒቴም ነው፤
3እግዚአብሔር ጠባቂዬ ነው፤ በእርሱም እታመናለሁ፤
ጋሻዬና የመድኀኒቴ ቀንድ፥ ረዳቴ፥ መጠጊያዬና መሸሸጊያዬ፥
መድኀኒቴ ሆይ፥ ከግፈኛ ታድነኛለህ።
4ምስጋና የሚገባውን እግዚአብሔርን እጠራለሁ፤
ከጠላቶቼም እድናለሁ።
5የሞት ጭንቅ ያዘኝ፤
የዐመፅ ጎርፍም አስፈራኝ፤
6የሞት ጣር ከበበኝ፤
የሞት ወጥመድም ደረሰብኝ።
7በጨነቀኝ ጊዜ እግዚአብሔርን ጠራሁት፤
እንዲረዳኝም ወደ አምላኬ ጮኽሁ፤
ከመቅደሱም ቃሌን ሰማኝ፤
ጩኸቴም በፊቱ ወደ ጆሮዎቹ ገባ።
8ምድርም ተንቀጠቀጠች፤ ተናወጠችም፤
የሰማይ መሠረቶችም ተነቃነቁ፤ ተንቀጠቀጡም፤
እግዚአብሔር ተቈጥቶአልና።
9ከቍጣው ጢስ ወጣ፤
ከአፉም የሚበላ እሳት ነደደ፤
ፍምም ከእርሱ ተቃጠለ።
10ሰማዮችን አዘነበለ፤ ወረደም፤
ጭጋግም ከእግሩ በታች ነበረ።
11በኪሩቤልም ላይ ተቀምጦ በረረ፤
በነፋስም ክንፎች ሆኖ ታየ፤
12መሰወርያውን ጨለማ አደረገ፤
በዙሪያውም የነበረውን ድንኳን የውኃ ጨለማ አደረገ፤
በደመናም አገዘፈው።
13በፊቱም ካለው ብርሃን የተነሣ ፍም ተቃጠለ።
14እግዚአብሔርም ከሰማይ አንጐደጐደ፤
ልዑልም ቃሉን ሰጠ።
15ፍላጻውን ላከ፤ በተናቸውም፤
መብረቅንም አሰምቶ አስደነገጣቸው።
16ከእግዚአብሔር ተግሣፅ የተነሣ፥
ከመዓቱም መንፈስ እስትንፋስ የተነሣ፥
የባሕር ፈሳሾች ታዩ፤
የዓለም መሠረቶችም ተገለጡ።
17ከላይ ላከ፤ ወሰደኝም፤
ከብዙ ውኆችም አወጣኝ።
18ከብርቱዎች ጠላቶቼ፥
ከሚጠሉኝም አዳነኝ፤ በርትተውብኝ ነበርና።
19በመከራዬ ቀን ደረሱብኝ፤
እግዚአብሔር ግን ደጋፊዬ ሆነ።
20ወደ ሰፊ ስፍራም አወጣኝ፤
ወድዶኛልና አዳነኝ።
21እግዚአብሔር እንደ ጽድቄ ይከፍለኛል፤
እንደ እጄ ንጽሕናም ይመልስልኛል፤
22የእግዚአብሔርን መንገድ ጠብቄአለሁና፥
በአምላኬም አላመፅሁምና።
23ፍርዱ ሁሉ በፊቴ ነበርና፤
ጽድቁም ከእኔ አልራቀምና።
24በእርሱ ዘንድ ንጹሕ እሆናለሁ፤
ከዐመፃዬም ራሴን እጠብቃለሁ።
25እግዚአብሔርም እንደ ጽድቄ፥
እንደ እጄም ንጽሕና በዐይኖቹ ፊት መለሰልኝ።
26ከጻድቅ ጋር ጻድቅ ትሆናለህ፤
ከንጹሕ ሰውም ጋር ንጹሕ ትሆናለህ፤
27ከተመረጠም ጋር የተመረጠ ትሆናለህ፤
ከጠማማ ጋርም ጠማማ ትሆናለህ።
28አንተ የተዋረደውን ሕዝብ ታድናለህና፤
የትዕቢተኞችን ዐይኖች ግን ታዋርዳለህ።
29አቤቱ! አንተ መብራቴ ነህና፤
እግዚአብሔርም ጨለማዬን ያበራልኛልና።
30በአንተ ብቻዬን እሮጣለሁና፤
በአምላኬም ቅጥሩን እዘልላለሁና።
31የኀያል አምላክ መንገድ ንጹሕ ነው፤
የእግዚአብሔር ቃል ጽኑዕ ነው፤
በእሳትም የጋለ ነው፤
በእርሱም ለሚታመኑት ጠባቂያቸው ነው።
32ከእግዚአብሔር በቀር ጽኑዕ ማን ነው?
ከአምላካችንስ በቀር ፈጣሪ ማን ነው?
33በኀይል የሚያጸናኝ ኀያል እርሱ ነው፤
መንገዴንም ንጹሕ አድርጎ አዘጋጀ፤
34እግሮቼን እንደ ዋልያ እግሮች አጸና፤
በኮረብቶችም አቆመኝ።
35ለእጆቼ ጦርነትን ያስተምራል፤
ለክንዴም የናስ ቀስት አዘዘ።
36የመድኀኒቴንም ጋሻ ሰጠኸኝ፤
መልስህም አበዛችኝ፤
37በሜዳም አረማመዴን በበታቼ አሰፋህ፤
እግሮቼም አልተንሸራተቱም።
38ጠላቶቼን አሳድዳቸዋለሁ፤ አጠፋቸውማለሁ፤
እስካጠፋቸውም ድረስ አልመለስም።
39እቀጠቅጣቸዋለሁ፤ መቆምም አይችሉም፤
ከእግሬም በታች ይወድቃሉ።
40በጦርነትም ጊዜ በኀይል ታጸናኛለህ፤
በላዬ የቆሙትንም በበታቼ ታስገዛቸዋለህ።
41የጠላቶቼን ጀርባ ሰጠኸኝ፤
የሚጠሉኝንም አጠፋሃቸው።
42ጮኹ፤ የሚረዳቸውም አልነበረም፤
ወደ እግዚአብሔር ጮኹ፤ አልሰማቸውምም።
43በነፋስ ፊት እንዳለ እንደ ምድር ትቢያ ፈጨኋቸው፤
እንደ ጎዳናም ጭቃ ረገጥኋቸው፤ ደቀደቅኋቸውም።
44ከአሕዛብ ጠብ አድነኝ፤
የአሕዛብም ራስ አድርገህ ትሾመኛለህ፤
የማላውቀው ሕዝብ ተገዛልኝ።
45የባዕድ ልጆች ዋሹኝ፤
በጆሮ ሰምተው መለሱልኝ።
46የባዕድ ልጆች አረጁ፤
ከማንከሳቸውም የተነሣ ተሰናከሉ።
47እግዚአብሔር ሕያው ነው፤ ጠባቂዬም ቡሩክ ነው፤
የሕይወቴ ጠባቂ አምላኬ ከፍ ከፍ ይበል፤
48በቀሌን የሚመልስልኝ አምላክ ጽኑዕ ነው።
አሕዛብን በበታቼ ያስገዛልኛል፤
49ከጠላቶቼ የሚያወጣኝ እርሱ ነው፤
በእኔም ላይ ከቆሙ ከፍ ከፍ ታደርገኛለህ፤
ከግፈኛም ሰው ታድነኛለህ።
50አቤቱ፥ ስለዚህ በአሕዛብ ዘንድ አመሰግንሃለሁ፥
ለስምህም እዘምራለሁ።
51የንጉሡን መድኀኒት ታላቅ ያደርጋል፤
ቸርነቱንም ለቀባው ለዳዊትና ለዘሩ፥
ለዘለዓለም ያደርጋል።”
Currently Selected:
መጽሐፈ ሳሙኤል ካልእ 22: አማ2000
ማድመቅ
ያጋሩ
ኮፒ
ያደመቋቸው ምንባቦች በሁሉም መሣሪያዎችዎ ላይ እንዲቀመጡ ይፈልጋሉ? ይመዝገቡ ወይም ይግቡ