መጽሐፈ ዜና መዋዕል ካልእ 7
7
የእግዚአብሔር ቤት ቅዳሴ መከበር
(1ነገ. 8፥62-66)
1ሰሎሞንም ይህን ጸሎት በፈጸመ ጊዜ እሳት ከሰማይ ወርዶ የሚቃጠለውን ቍርባንና መሥዋዕቱን ሁሉ በላ፤ የእግዚአብሔርም ክብር ቤቱን ሞላ። 2የእግዚአብሔርም ክብር የእግዚአብሔርን ቤት ሞልቶት ነበርና ካህናቱ በዚያች ዕለት ወደ እግዚአብሔር ቤት መግባት አልቻሉም። 3የእስራኤልም ልጆች ሁሉ እሳቱ ሲወርድ የእግዚአብሔርም ክብር በቤቱ ላይ ሲሆን ያዩ ነበር፤ ድንጋይ በተነጠፈበትም ምድር በግንባራቸው ተደፍተው ሰገዱ፥ “እርሱ ቸር ነውና፥ ምሕረቱም ለዘለዓለም ነውና” እያሉ እግዚአብሔርን አመሰገኑ።
4ንጉሡም ሰሎሞን፥ የእስራኤልም ሕዝብ ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት መሥዋዕት ያቀርቡ ነበር። 5በዚያችም ዕለት ንጉሡ ሰሎሞን ሃያ ሁለት ሺህ በሬዎችንና መቶ ሃያ ሺህ በጎችን ሠዋ። እንዲሁ ንጉሡና ሕዝቡ ሁሉ የእግዚአብሔርን ቤት ቅዳሴ አከበሩ። 6ካህናቱም በየሥርዐታቸው ሌዋውያኑም ደግሞ፥ “ምሕረቱ ለዘለዓለም ነውና እግዚአብሔርን አመስግኑ” የሚለውን የዳዊትን መዝሙር እየዘመሩ፥ ንጉሡ ዳዊት እግዚአብሔርን ለማመስገን የሠራውን የእግዚአብሔርን የዜማ ዕቃ ይዘው ቆመው ነበር፤ ካህናቱም በፊታቸው መለከት ይነፉ ነበር፤ እስራኤልም ሁሉ ቆመው ነበር። 7ሰሎሞንም በእግዚአብሔር ቤት ፊት የነበረውን የአደባባዩን ውስጥ ቀደሰ፤ ሰሎሞንም የሠራው የናስ መሠዊያ የሚቃጠለውን መሥዋዕትና የእህሉን ቍርባን፥ ስቡንም መያዝ አልቻለምና የሚቃጠለውን መሥዋዕትና የደኅንነቱንም መሥዋዕት፥ ስብ በዚያ አቀረበ።
8ሰሎሞንም፥ ከእርሱም ጋር እጅግ ታላቅ ጉባኤ የሆኑ ከኤማት መግቢያ ጀምሮ እስከ ግብፅ ወንዝ ድረስ ያሉ እስራኤል ሁሉ፥ በዚያ ጊዜ ሰባት ቀን በዓል አደረጉ። 9መሠዊያውንም ቀድሶ፥ ሰባት ቀን በዓል አድርጎ ነበርና በስምንተኛው ቀን የፍጻሜ በዓል አደረገ። 10በሰባተኛውም ወር በሃያ ሦስተኛው ቀን ሕዝቡን ወደ ድንኳናቸው አሰናበተ፤ እግዚአብሔር ለዳዊትና ለሰሎሞን፥ ለሕዝቡም ለእስራኤል ስላደረገው ቸርነት በልባቸው ደስ ብሎአቸው ሄዱ።
11ሰሎሞንም የእግዚአብሔርን ቤትና የንጉሡን ቤት፥ በእግዚአብሔር ቤትና በራሱ ቤት ይሠራው ዘንድ በልቡ ያሰበውን ሁሉ ጨረሰ፤ አከናወነም። 12እግዚአብሔርም ለሰሎሞን በሌሊት ተገልጦ እንዲህ አለው፥ “ ጸሎትህን ሰምቻለሁ፤ ይህንም ስፍራ ለራሴ ለመሥዋዕት ቤት መርጫለሁ። 13ዝናብ እንዳይወርድ ሰማያቱን ብዘጋ፥ ወይም የሚያፈራውን እንጨት ሁሉ ይበላ ዘንድ አንበጣን ባዝዘው፥ ወይም በሕዝቤ ላይ ቸነፈር ብሰድድ፥ 14በስሜ የተጠሩት ሕዝቤ ሰውነታቸውን አዋርደው ቢጸልዩ፥ ፊቴንም ቢፈልጉ፥ ከክፉ መንገዳቸውም ቢመለሱ፥ በሰማይ ሆኜ እሰማለሁ፥ ኀጢአታቸውንም ይቅር እላለሁ፤ ምድራቸውንም እፈውሳለሁ። 15አሁንም በዚህ ስፍራ ለሚጸለይ ጸሎት ዐይኖች ይገለጣሉ፤ ጆሮዎችም ያዳምጣሉ። 16አሁንም ስሜ ለዘለዓለም በዚያ ይኖር ዘንድ ይህን ቤት መርጫለሁ፤ ቀድሻለሁም፤ ዐይኖችና ልቤም ዘወትር በዚያ ይሆናሉ። 17አንተም ደግሞ አባትህ ዳዊት እንደ ሄደ በፊቴ ብትሄድ፥ እንዳዘዝሁም ሁሉ ብታደርግ፥ ሥርዐቴንና ፍርዴንም ብትጠብቅ፥ 18ከአባትህ ከዳዊት ጋር፦ ‘በእስራኤል ላይ አለቃ የሚሆን ከዘርህ አይታጣም’ ብዬ ቃል ኪዳን እንዳደረግሁ የመንግሥትህን ዙፋን አጸናለሁ።
19“እናንተ ግን ብትመለሱ፥ የሰጠኋችሁን ሥርዐቴንና ትእዛዜን ብትተዉ፥ ሄዳችሁም ሌሎችን አማልክት ብታመልኩ፥ ብትሰግዱላቸውም፥ 20እኔም ለአባቶቻችሁ ከሰጠኋቸው ምድር እነቅላችኋለሁ፤ ለስሜም የቀደስሁትን ይህን ቤት ከፊቴ እጥለዋለሁ፤ በአሕዛብም ሁሉ መካከል ምሳሌና ተረት አደርገዋለሁ። 21ከፍ ከፍ ብሎ የነበረውንም ይህን ቤት እያየ በዚያ የሚያልፍ መንገደኛ ሁሉ፦ ‘እግዚአብሔር በዚህ ሀገርና በዚህ ቤት ስለ ምን እንዲህ አደረገ?’ ብሎ ይደነቃል። 22መልሰውም፦ ከግብፅ ምድር ያወጣቸውን ያባቶቻቸውን አምላክ እግዚአብሔርን ትተው ሌሎችን አማልክት ስለ ተከተሉ፥ ስለ ሰገዱላቸውም፥ ስለ አመለኩአቸውም፥ ስለ አገለገሏቸውም፥ ስለዚህ ይህን ክፉ ነገር ሁሉ አመጣባቸው” ይላሉ።
Currently Selected:
መጽሐፈ ዜና መዋዕል ካልእ 7: አማ2000
ማድመቅ
ያጋሩ
ኮፒ

ያደመቋቸው ምንባቦች በሁሉም መሣሪያዎችዎ ላይ እንዲቀመጡ ይፈልጋሉ? ይመዝገቡ ወይም ይግቡ