ሰቈቃወ ኤርምያስ 3
3
1አሌፍ። በቁጣው በትር መከራ ያየ ሰው እኔ ነኝ።
2ብርሃን ወደሌለበት ወደ ጨለማ መርቶ ወሰደኝ።
3ዘወትር ቀኑን ሁሉ እጁን በላዬ መለሰ።
4ቤት። ሥጋዬንና ቁርበቴን አስረጀ፥ አጥንቴን ሰበረ።
5ቅጥር ሠራብኝ በሐሞትና በድካምም ከበበኝ።
6ቀድሞ ሞተው እንደ ነበሩ በጨለማ አኖረኝ።
7ጋሜል። እንዳልወጣ በዙሪያዬ ቅጥር ሠራብኝ፥ ሰንሰለቴን አከበደ።
8በጠራሁና በጮኽሁ ጊዜ ጸሎቴ ከለከለ።
9መንገዴን በተጠረበ ድንጋይ ዘጋ፥ ጐዳናዬንም አጣመመ።
10ዳሌጥ። እንደሚሸምቅ ድብ እንደ ተሸሸገም አንበሳ ሆነብኝ።
11መንገዴን ለወጠ፥ ገነጣጠለኝም፥ ባድማ አደረገኝ።
12ቀስቱን ገተረ ለፍላጻውም እንደ ጊጤ አደረገኝ።
13ሄ። የሰገባውን ፍላጻዎች በኩላሊቴ ውስጥ ተከለ።
14ለወገኔ ሁሉ ማላገጫ ቀኑንም ሁሉ መሳለቂያ ሆንሁ።
15ምሬት ሞላብኝ በእሬትም አጠገበኝ።
16ዋው። ጥርሴን በጭንጫ ሰበረ፥ በአመድም ከደነኝ።
17ነፍሴን ከሰላም አራቅህ፥ በጎ ነገርን ረሳሁ።
18እኔም፦ ኃይሌ ከእግዚአብሔርም ዘንድ ያለው ተስፋዬ ጠፋ አልሁ።
19ዛይ። መከራዬንና ችግሬን እሬትንና ሐሞትን አስብ።
20ነፍሴ እያሰበችው በውስጤ ፈዘዘች።
21ይህችን በልቤ አኖራለሁ፥ ስለዚህ እታገሣለሁ።
22ሔት። ያልጠፋነው ከእግዚአብሔር ምሕረት የተነሣ ነው፥ ርኅራኄው አያልቅምና።
23ማለዳ ማለዳ አዲስ ነው፥ ታማኝነትህ ብዙ ነው።
24ነፍሴ፦ እግዚአብሔር እድል ፈንታዬ ነው፥ ስለዚህ ተስፋ አደርገዋለሁ አለች።
25ጤት። ጌታ በተስፋ ለሚጠብቁት ለምትሻውም ነፍስ መልካም ነው።
26ሰው ዝም ብሎ የእግዚአብሔርን ማዳን ተስፋ ቢያደርግ መልካም ነው።
27ሰው በታናሽነቱ ቀንበር ቢሸከም መልካም ነው።
28ዮድ። እርሱ አሸክሞታልና ዝም ብሎ ለብቻው ይቀመጥ።
29ተስፋ የሆነው እንደሆነ አፉን በአፈር ውስጥ ያኑር።
30ጉንጩን ለሚመታው ይስጥ፥ ስድብንም ይጥገብ።
31ካፍ። ጌታ ለዘለዓለም አይጥልምና፥
32ቢያሳዝንም እንደ ምሕረቱ ብዛት ይራራልና፥
33የሰውን ልጆች ከልቡ አያስጨንቅም፥ አያሳዝንምም።
34ላሜድ። በምድር የተጋዙትን ሁሉ ከእግሩ በታች ይረግጣቸው ዘንድ፥
35የሰውን ፍርድ በልዑል ፊት ይመልስ ዘንድ፥
36የሰውን ፍርድ ያጣምም ዘንድ ጌታ እሺ አይልም።
37ሜም። ጌታ ያላዘዘውን የሚልና የሚፈጽም ማን ነው?
38ከልዑል አፍ ክፉና መልካም ነገር አይወጣምን?
39ሕያው ሰው የሚያጉረመርም፥ ሰው ስለ ኃጢአቱ ቅጣት የሚያጉረመርም ስለ ምንድነው?
40ኖን። መንገዳችንን እንመርምርና እንፈትን፥ ወደ እግዚአብሔርም እንመለስ።
41ልባችንን ከእጃችን ጋር በሰማይ ወዳለው ወደ እግዚአብሔር እናንሣ።
42በድለናል ዐምፀናልም፥ አንተም ይቅር አላልህም።
43ሳምኬት። በቁጣ ከደንኸን አሳደድኸንም፥ ገደልኸን፥ አልራራህም።
44ጸሎት እንዳያልፍ ራስህን በደመና ከደንህ።
45በአሕዛብ መካከል ጉድፍና ውዳቂ አደረግኸን።
46ዔ። ጠላቶቻችን ሁሉ አፋቸውን ኣላቀቁብን።
47ድንጋጤና ቁጣ፥ ጥፋትና ቅጥቃጤ ሆነብን።
48ስለ ወገኔ ሴት ልጅ ቅጥቃጤ ዓይኔ የውኃ ፈሳሽ አፈሰሰች።
49-50ፌ። እግዚአብሔር ከሰማይ እስኪጐበኝና እስኪመለከት ድረስ
ዓይኔ ሳታቋርጥ ዝም ሳትል እንባ ታፈስሳለች።
51ስለ ከተማዬ ቈነጃጅት ሁሉ ዓይኔ ነፍሴን አሳዘነች።
52ጻዴ። በከንቱ ነገር ጠላቶች የሆኑኝ እንደ ወፍ ማደንን አደኑኝ።
53ሕይወቴን በጉድጓድ አጠፉ፥ በላዬም ድንጋይ ጣሉ።
54በራሴ ላይ ውኆች ተከነበሉ፥ እኔም፦ ጠፋሁ ብዬ ነበር።
55ቆፍ። አቤቱ፥ በጠለቀ ጉድጓድ ውስጥ ሆኜ ስምህን ጠራሁ።
56ድምፄን ሰማህ፥ ጆሮህን ከልመናዬ አትመልስ።
57በጠራሁህ ቀን ቀርበህ፦ አትፍራ አልህ።
58ሬስ። ጌታ ሆይ፥ ስለ ነፍሴ ተምዋግተህ ሕይወቴን ተቤዠህ።
59አቤቱ፥ ጭንቀቴን አይተሃል፥ ፍርዴን ፍረድልኝ።
60በቀላቸውን ሁሉና በእኔ ላይ ያለውን አሳባቸውን ሁሉ አየህ።
61ሳን። አቤቱ፥ ስድባቸውንና በእኔ ላይ ያለውን አሳባቸውን ሁሉ፥
62የተነሡብኝን ሰዎች ከንፈሮች ቀኑንም ሁሉ ያሰቡብኝን አሳባቸውን ሰማህ።
63መቀመጣቸውንና መነሣታቸውን ተመልከት፥ እኔ መሳለቂያቸው ነኝ።
64ታው። አቤቱ፥ እንደ እጃቸው ሥራ ፍዳቸውን ትከፍላቸዋለህ።
65የልብ ዕውርነትንና እርግማንህን ትሰጣቸዋለህ።
66አቤቱ፥ በቁጣ ታሳድዳቸዋለህ ከሰማይም በታች ታጠፋቸዋለህ።
Currently Selected:
ሰቈቃወ ኤርምያስ 3: መቅካእኤ
ማድመቅ
ያጋሩ
ኮፒ

ያደመቋቸው ምንባቦች በሁሉም መሣሪያዎችዎ ላይ እንዲቀመጡ ይፈልጋሉ? ይመዝገቡ ወይም ይግቡ