ጠዋት በማለዳ የካህናት አለቆችና የሕዝብ ሽማግሌዎች ሁሉ በኢየሱስ ላይ የሞት ፍርድ ለማስፈረድ ተማከሩ። ከዚህ በኋላ ኢየሱስን አስረው ወሰዱና ለገዥው ለጲላጦስ አሳልፈው ሰጡት። ኢየሱስ እንደተፈረደበት ባየ ጊዜ አሳልፎ የሰጠው ይሁዳ ተጸጸተ፤ ሠላሳውንም ጥሬ ብር ለካህናት አለቆችና ሽማግሌዎች እንዲህ በማለት መልሶ ሰጣቸው፤ “ንጹሑን ሰው ለሞት አሳልፌ በመስጠቴ በድዬአለሁ።” እነርሱ ግን “ታዲያ፥ እኛ ምን ቸገረን! የራስህ ጉዳይ ነው!” አሉት። እርሱም ሠላሳውን ጥሬ ብር በቤተ መቅደስ ውስጥ በትኖ፥ ትቶአቸው ወጣ፤ ሄዶም ታንቆ ሞተ። የካህናት አለቆች ሠላሳውን ጥሬ ብር አንሥተው “ይህ ገንዘብ የደም ዋጋ ስለ ሆነ ከቤተ መቅደስ መባ ጋር ልንቀላቅለው አይፈቀድም” አሉ። ስለዚህ ከተመካከሩ በኋላ ለእንግዶች የመቃብር ቦታ እንዲሆን የሸክላ ሠሪውን መሬት ገዙበት። በዚህ ምክንያት ያ መሬት እስከ ዛሬ ድረስ “የደም መሬት” እየተባለ ይጠራል። በዚህ ሁኔታ “የእስራኤል ልጆች የገመቱትን ለእርሱ ዋጋ የሚሆን ሠላሳ ጥሬ ብር ወሰዱ፤ ጌታም እንዳዘዘኝ ስለ ሸክላ ሠሪው መሬት ከፈሉት” ተብሎ በነቢዩ ዘካርያስ የተነገረው ትንቢት ተፈጸመ። በዚያን ጊዜ ኢየሱስ ወደ ገዢው ወደ ጲላጦስ ፊት ቀረበ፤ ገዢውም “አንተ የአይሁድ ንጉሥ ነህን?” ሲል ጠየቀው፤ ኢየሱስም “አንተ እንዳልከው ነው” ሲል መለሰ። ነገር ግን የካህናት አለቆችና ሽማግሌዎች ሲወነጅሉት ምንም መልስ አልሰጠም። ከዚህ በኋላ ጲላጦስ “በስንት ነገር ሲወነጅሉህ አትሰማምን?” አለው። ኢየሱስ ግን ገዢው እስኪደነቅ ድረስ ለአንዲት ክስ እንኳ ቃል አልመለሰለትም።
የማቴዎስ ወንጌል 27 ያንብቡ
ያጋሩ
ሁሉንም ሥሪቶች ያነጻጽሩ: የማቴዎስ ወንጌል 27:1-14
ጥቅሶችን ያስቀምጡ፣ ያለበይነመረብ ያንብቡ፣ አጫጭር የትምህርት ቪዲዮዎችን ይመልከቱ እና ሌሎችም!
ቤት
መጽሐፍ ቅዱስ
እቅዶች
ቪዲዮዎች