ማቴዎስ 14:13-21

ማቴዎስ 14:13-21 NASV

ኢየሱስ የሆነውን ነገር በሰማ ጊዜ፣ ከነበረበት ተነሥቶ ወደ አንድ ገለልተኛ ስፍራ በጀልባ ሄደ። ሕዝቡም ይህን ሰምተው፣ ከየከተማው በእግር ተከተሉት። ኢየሱስም ከጀልባው ሲወርድ ብዙ ሕዝብ አይቶ ራራላቸው፤ ሕመምተኞቻቸውንም ፈወሰላቸው። ሊመሽ ሲል ደቀ መዛሙርቱ ወደ እርሱ ቀርበው፣ “ይህ ስፍራ ምንም የማይገኝበት ምድረ በዳ ነው፤ ጊዜው እየመሸ ስለ ሆነ፣ ወደ መንደሮች ሄደው የሚበሉት ምግብ እንዲገዙ ሕዝቡን አሰናብት” አሉት። ኢየሱስ ግን፣ “መሄድ አያስፈልጋቸውም፤ የሚበሉትን እናንተ ስጧቸው” አላቸው። እነርሱም፣ “በዚህ ያለን ዐምስት እንጀራና ሁለት ዓሣ ብቻ ነው” አሉት። እርሱም፣ “እስኪ ያለውን ወደ እኔ አምጡት” አላቸው። ከዚያም ሕዝቡ በሣሩ ላይ እንዲቀመጡ አዘዘ፤ ዐምስቱን እንጀራና ሁለቱን ዓሣ ይዞ ዐይኑን ወደ ሰማይ በማቅናት አመስግኖና ባርኮ እንጀራውን ቈረሰ፤ ለደቀ መዛሙርቱም ሰጠ፤ እነርሱም ለሕዝቡ ሰጡ። ሁሉም በልተው ጠገቡ፤ ከዚያም ደቀ መዛሙርቱ የተረፈውን ቍርስራሽ ዐሥራ ሁለት መሶብ ሙሉ አነሡ። የበሉትም ከሴቶችና ከሕፃናት ሌላ፣ ዐምስት ሺሕ ወንዶች ያህሉ ነበር።

ተዛማጅ ቪዲዮዎች